የሳይበር ደህንነትን ማስጠበቅ የሀገር ሉዓላዊነት ጉዳይ መሆኑን መገንዘብ ይገባል - ኢዜአ አማርኛ
የሳይበር ደህንነትን ማስጠበቅ የሀገር ሉዓላዊነት ጉዳይ መሆኑን መገንዘብ ይገባል

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 1/2018(ኢዜአ)፦ የሳይበር ደህንነት ጉዳይ ከሀገር ሉዓላዊነት ጋር የሚተሳሰር መሆኑን በመገንዘብ በዘርፉ የሚከናወኑ ቅንጅታዊ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለም ፀሐይ ጳውሎስ ገለፁ።
6ተኛው ሀገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር ማስጀመሪያ ስነ ሥርዓት እየተካሄደ ይገኛል።
የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምፀሐይ ጳውሎስ ባስተላለፉት መልእክት ባለፉት የለውጥ ዓመታት በሁሉም ዘርፎች ስኬታማ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል።
የኢትዮጵያ የማንሰራራት ጅማሮ ማሳያ የሆኑ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን ጨምሮ የተመረቁና የተጀመሩ ግዙፍ ፕሮጀክቶች መንግስት ለዘላቂ ልማትና እድገት ያለውን ቁርጠኝነት በተግባር ያሳዩ ናቸው ብለዋል።
የዜጎችን የዕለት ተዕለት የህይወት እንቅስቃሴና የመንግሥትን አገልግሎት የሚያሳልጡ የዲጂታል አሠራሮችን በመተግበር ተጨባጭ ለውጦች መምጣታቸውን አንስተዋል።
በአሁኑ ወቅት ከ900 በላይ የሚሆኑና በተቋማት የሚሰጡ አገልግሎቶች በቴክኖሎጂ አማካይነት ለተገልጋዮች ተደራሽ እየተደረጉ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ቴክኖሎጂና ልማት ተሰናስለው የሚሔዱ ናቸው ያሉት ሚኒስትሯ፥ የልማት ስራዎቹ ደህንነታቸው ተጠብቆ እንዲቆይ ማድረግ ላይ ትኩረት ሰጥቶ መስራት ወሳኝ መሆኑን ገልፀዋል።
የሳይበር ደህንነት ጉዳይ ከሀገር ሉአላዊነት ጋር የሚተሳሰር በመሆኑ በዘርፉ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸውም አሳስበዋል።
ለዚህም በተለያዩ አማራጮች ተደራሽ የሚደረጉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች ጉልህ ሚና እንዳላቸው ነው የጠቆሙት።
የሳይበር ደህንነት ወር እንደ ሀገር በሳይበር ደህንነት ላይ የሚከናወኑ ተግባራትን በስፋት ለማስገንዘብ እድል የሚፈጥርና የተቋማትን ቅንጅታዊ አሰራር ለማጠናከር የሚያግዝ ነው ብለዋል።
በመሆኑም በመላ ሀገሪቱ በሳይበር ደህንነት ዙሪያ የሚከናወኑ ተግባራት ውጤታማ በሆነ መልኩ ተግባራዊ ለማድረግ ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንሚገባ አስገንዝበዋል።