በተፈጥሮ ጋዝ የሚሰሩ የደረቅና የፈሳሽ ጭነት እንዲሁም የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች ከጉምሩክ ቀረጥ ነጻ ወደ ሀገር እንዲገቡ ተፈቀደ - ኢዜአ አማርኛ
በተፈጥሮ ጋዝ የሚሰሩ የደረቅና የፈሳሽ ጭነት እንዲሁም የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች ከጉምሩክ ቀረጥ ነጻ ወደ ሀገር እንዲገቡ ተፈቀደ

አዲስ አበባ፤ መስከረም 30/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት በተፈጥሮ ጋዝ የሚሰሩ ማናቸውም አይነት የደረቅ እና የፈሳሽ ጭነት እና የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች ከጉምሩክ ቀረጥ ነጻ ወደ ሀገር እንዲገቡ መፍቀዱን የገንዘብ ሚኒስቴር አስታወቀ።
ኢትዮጵያ ከፍተኛ መጠን ያለው የተፈጥሮ ጋዝ ክምችት ያላት መሆኑ ቢታወቅም ለዘመናት የዚህ የተፈጥሮ ሃብት ተጠቃሚ ሳትሆን መቆየቷን ሚኒስቴሩ ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
ይህንን ሁኔታ ለመለወጥ መንግስት ሲያደርግ የቆየው እልህ አስጨራሽ ጥረት ተሳክቶ በቅርቡ በካሉብ አካባቢ የሚገኘውን የተፈጥሮ ጋዝ ጥቅም ላይ ማዋል የሚያስችል ኢንዱስትሪ ተመርቆ የተፈጥሮ ጋዝ የማምረት ስራ በይፋ መጀመሩን ገልጿል።
ይህን ምርት ለሀገር ውስጥ ገበያ በማቅረብ ቤንዚንና ናፍታ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን የተፈጥሮ ጋዝ በሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎች መተካት አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱን አንስቷል።
የተፈጥሮ ጋዝ የሚያመነጨው በካይ አየር እጅግ በጣም ዝቅተኛ የሆነ፤ ለተለያየ የኃይል ምንጭ አገልግሎት ሊውል የሚችል፤ በኃይል አጠቃቀም ረገድ ውጤታማነት ያለው መሆኑን መረጃው ያመለከተው።
የተፈጥሮ ጋዝ በኢትዮጵያ የሚመረት በመሆኑ ለነዳጅ ግዥ ታወጣ የነበረውን የውጭ ምንዛሬ የሚያስቀር በመሆኑ መንግስት የተፈጥሮ ጋዝ አጠቃቀምን ለማበረታታት ወስኗል።
በዚህም መሰረት ይህ መመሪያ ከወጣበት ቀን ጀምሮ ሙሉ በሙሉ በተፈጥሮ ጋዝ የሚሰሩ ማናቸውም አይነት የደረቅ እና የፈሳሽ ጭነት እና የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች ከጉምሩክ ቀረጥ ነጻ ወደ ሀገር እንዲገቡ መፈቀዱን ሚኒስቴሩ አስታውቋል።
ስለዚህ በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር በተወሰነው መሰረት ይህ መመሪያ ከወጣበት ቀን በፊት በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር እና በሌሎች ተቋማት ወደ ሀገር እንዲገቡ ከተፈቀደላቸውና በስድስት ወር ጊዜ ውስጥ ወደ ሀገር ከሚገቡት በስተቀር በቤንዚን እና በናፍጣ የሚሰሩ የጭነት እና የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች ወደ ሀገር እንዳይገቡ ጥብቅ ቁጥጥር እንዲደረግ ሚኒስቴሩ አሳስቧል።