ቀጥታ፡

የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፈጣን፣ ግልጽ እና ውጤታማ የሆነ ሥርዓት ለመገንባት በጽናት እየሠራ ይገኛል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ መስከረም 30/2018(ኢዜአ)፡- የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፈጣን፣ ግልጽ እና ውጤታማ የሆነ ሥርዓት ለመገንባት በጽናት እየሠራ ይገኛል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፤ ቴክኖሎጂ መር አዘማኝነት ላይ የሚያተኩረው የዲጂታል 2025 ስትራቴጂ በስኬት መጠናቀቅን ተከትሎ አሁን በበለጠ የማሽን ግብዓት(አቶሜሽን) በመጠቀም አገልግሎት አሰጣጥን የሚያጠናክረውን ዲጂታል 2030ን አስጀምረናል ብለዋል።


 

የፍትኅ ተደራሽነት ለዜጎች እጅግ አስፈላጊ ከሆኑ ጉዳዮች አንዱ መሆኑን እውቅና በመሥጠትም የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፈጣን፣ ግልጽ እና ውጤታማ የሆነ ሥርዓት ለመገንባት በጽናት እየሠራ ይገኛል ነው ያሉት።

ዛሬ የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የፍርድ ሂደቶች በአግባቡ መቀዳታቸውን ለማረጋገጥ ድምጽን ወደ ጽሁፍ የሚቀይር ብሎም በአስተማማኝ ሁኔታ ተጠብቀው የሚቆዩበትን ስማርት የፍርድ ሥርዓት አልምቶ በመመልከቴ ደስታ ተሰምቶኛል ብለዋል በመልዕክታቸው።

ሥርዓቱ ፍትኅ ፈላጊዎች ወደ አዲስ አበባ ተጉዘው በአካል በችሎት መገኘት ሳይጠበቅባቸው ካሉበት ሆነው ጉዳያቸውን መከታተል እንደሚያስችላቸውም ነው ያስታወቁት።


 

በተጨማሪም የለሙት የNetwork Operation Center እና Integrated Case Management System የፍርድ ሂደት ባለጉዳዮች በዲጂታል አውታሮች ጉዳያቸውን እንዲከታተሉ ያስችላሉ ብለዋል።

በአሁኑ ወቅት 24 የፌደራል ቅርንጫፎች በሥርዓቱ የተሸፈኑ መሆኑ አበረታች መሆኑን ጠቅሰው በቅርቡ ወደ ክልሎችም እንደሚስፋፋ ተስፋ አለን ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም