የአስተዳደር ወሰንና የማንነት ጥያቄዎች ሕገ-መንግስታዊና ሕጋዊ አሰራርን በተከተለ አግባብ ምላሽ እንዲያገኙ ይደረጋል - ኢዜአ አማርኛ
የአስተዳደር ወሰንና የማንነት ጥያቄዎች ሕገ-መንግስታዊና ሕጋዊ አሰራርን በተከተለ አግባብ ምላሽ እንዲያገኙ ይደረጋል

አዲስ አበባ፤ መስከረም 28/2018(ኢዜአ)፦ የአስተዳደር ወሰንና የማንነት ጥያቄዎች ሕገ-መንግስታዊና ሕጋዊ አሰራርን በተከተለ አግባብ ሕብረ ብሔራዊ አንድነትን በሚያጠናክር መልኩ ምላሽ እንዲያገኙ እንደሚደረግ በፌዴሬሽን ምክር ቤት የማንነት፣ የአስተዳደር ወሰንና የሰላም ግንባታ ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ።
የፌዴሬሽን ምክር ቤት በ6ኛ የፓርላማ ዘመን 5ኛ ዓመት የሥራ ጊዜ 1ኛ መደበኛ ስብሰባ የማንነት፣ አስተዳደር፣ ወሰንና ሰላም ግንባታ ቋሚ ኮሚቴ የ2017 ዓ.ም በጀት ዓመት የዕቅድ አፈፃጸም ሪፖርትን በማዳመጥ የ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ዕቅድ ላይ ተወያይቶ አጽድቋል።
የቋሚ ኮሚቴው ጸሐፊ አቶ ፍቅሬ አማን፥ በህዝቦች በሚቀርቡ የማንነት፣ አስተዳደር ወሰንና ሠላም ግንባታ ጉዳዮች ላይ የተከናወኑ ተግባራት ከዚህ ቀደም ከሚቀርቡት አንፃር ሲታይ እየቀነሱ ነው ብለዋል።
በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ለሚቀርቡ የማንነት ይታወቅልኝና የህዝብ ውክልና አቤቱታዎች በጥናት ላይ የተመሰረተ ምላሽ ለመስጠት በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል።
የብሔር፣ብሔረሰቦችና ህዝቦች የማንነት መገለጫ (አትላስ) ጥናትን ለማስጀመር ከባለድርሻ አካላት ጋር የተጀመሩ የምክክር መድረኮችን በማስቀጠል ቀሪ ተግባራት በማጠናቀቅ ወደስራ እንደሚገባም ተናግረዋል።
በአስተዳደር ወሰንና እራስን በራስ የማስተዳደር የሚነሱ ጥያቄዎች ሕገ-መንግስታዊና ሕጋዊ አሰራርን በተከተለ አግባብ ሕብረ ብሔራዊ አንድነትን በሚያጠናክር መልኩ ምላሽ እንዲያገኙ ይደረጋል ብለዋል።
በሁሉም ክልሎች የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትንና የሰላም እሴት ግንባታ ስራዎችን የሚያጠናክሩ የምክክር መድረኮች በስፋት ለማካሄድ መታቀዱንም አስረድተዋል።
በምክር ቤቱ ቀርበው የነበሩና ወደክልሎች የተላኩ አቤቱታዎችን አፈፃፀም በመገምገም የድጋፍና ክትትል ስራዎችን በማከናወን ህዝቦች የሚያነሷቸውን ጥያቄዎች ምላሽ እንዲያገኙ ይደረጋል ብለዋል።
የምክር ቤቱ አባላት በበኩላቸው፤ የማንነት ይታወቅልኝና የአስተዳደር ወሰን ጥያቄዎች ከጊዜ ወደጊዜ እየቀነሰ መምጣቱ መንግስት የህዝቦችን ጥያቄ ተገቢ የመልካም አስተዳደር ምላሽ እየሰጠ መሆኑን የሚሳይ እንደሆነ ገልጸዋል።
በቀጣይም በአማራና ትግራይ፣ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልልና ሲዳማ፣ በጋምቤላና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች የሚነሱ የማንነትና የአስተዳደር ወሰን ጥያቄዎች የህዝብን አንድነት በሚያጠናክር መልኩ ምላሽ እንዲያገኙ መስራት እንደሚያስፈልግ ጠይቀዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እና የማንነት፣የአስተዳደር ወሰንና የሰላም ግንባታ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ጥላሁን ከበደ፥ የተፈጸሙ፣ ያልተፈፀሙና ለግጭት መንስኤ የሆኑ ጉዳዮችን ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት የማንነት፣አስተዳደር፣ ወሰንና ሰላም ግንባታ ስራዎችን ምላሽ ለመስጠት እየተሰራ ነው ብለዋል።
በዚህም ህዝቦች የሚያነሷቸው ጥያቄዎች አንድነትና ወንድማማችነትን በሚያጠናክር መልኩ ሕገመንግስታዊና ህጋዊ ምላሽ እንደሚሰጣቸው ገልጸዋል።
በፌዴሬሽን ምክር ቤት የማንነት፣የአስተዳደር ወሰንና የሰላም ግንባታ ቋሚ ኮሚቴ ጸሐፊ አቶ ፍቅሬ አማን፥ በአማራና ትግራይ አዋሳኝ አካበቢዎች የሚነሳውን የማንነትና የአስተዳደር ወሰን ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት በመንግስት ደረጃ ግልጽ አቅጣጫ ተቀምጦ እየተሰራበት ነው ብለዋል።
በሁሉም አካባቢዎች የሚነሱ የማንነትና የአስተዳደር ወሰን ጉዳዮችን ሕጋዊና ሕገ-መንግስታዊ አሰራርን በተከተለ አግባብ ምላሽ የመስጠት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።