ቀጥታ፡

በሐረሪ ክልል እቅድን መሰረት ያደረጉ ተግባራት በውጤታማነት እንዲፈጸሙ ይደረጋል - ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ

ሐረር፤ መስከረም 20/2018 (ኢዜአ) ፡- በሐረሪ ክልል እቅድን መሰረት ያደረጉ ተግባራት ተፈጻሚ ሆነው የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለጹ።

ርዕሰ መስተዳድሩ እና የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) በተገኙበት በክልላዊ የኢኮኖሚ አካውንት፣ በኢትዮጵያ ስታቲስትክስ ፕሮግራም እና በዲጂታል ልማት እንዲሁም በመንግስት የልማት ፕሮጀክቶች አመራርና አስተዳደር አተገባበር ዙሪያ ምክክር እየተካሄደ ነው።


 

በወቅቱም ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ እንደተናገሩት፤ የህዝብን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራትን ይበልጥ ተፈጻሚ ለማድረግ እቅድን መሰረት በማድረግ ስራዎችን ማጠናከር ተገቢ ነው።

በተለይም ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ጥራት ያለው እቅድ ማዘጋጀትና እቅዱን ደግሞ በአግባቡ መፈፀም ለበለጠ ውጤታማነት ያግዛል ብለዋል።

በክልሉ የተሻለ እና ውጤታማ ስራ በጋራ ለማከናወንና የማንሰራራት ዘመንን ለማስቀጠል በእቅድ መመራት ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ገልጸዋል።

ወቅቱን የጠበቀና ትክክለኛ እና ተዓማኒነት ያለው መረጃ ተደራሽ ለማድረግ፣ ትክክለኛ ፖሊሲ ለማውጣት እንዲሁም ውሳኔ ለመስጠት የእቅድ ዝግጅት ትግበራም እንዲሁ።

የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ከለውጡ ማግስት ጀምሮ ፕሮጀክቶችን የማስተዳደርና የመፈጸም አቅም ማደጉን አንስተዋል።

በቀጣይም በክልላዊ የኢኮኖሚ አካውንት፣ በኢትዮጵያ ስታቲስትክስ ፕሮግራም እና በዲጂታል ልማት ዙሪያ የተጀመሩ ስራዎችን በማጠናከርና ወደ ክልሎች በማውረድ ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ ለመፍጠር እንደሚሰራ ተናግረዋል።

ለዚህም ሚኒስቴሩ ከክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ጋር የተቀናጁ ተግባራትን እንደሚያከናውን ገልጸዋል።


 

በአሁኑ ወቅት የተለያዩ ፅሁፎች ቀርበው ውይይት እየተደረገባቸው ይገኛል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም