ከ5 ሚሊዮን በላይ ወጣቶች በዲጂታል ዕውቀትና ክህሎት ላይ ያተኮረ የኦንላይን ቢዝነስ ስልጠና እንዲያገኙ ይደረጋል - የአማራ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ - ኢዜአ አማርኛ
ከ5 ሚሊዮን በላይ ወጣቶች በዲጂታል ዕውቀትና ክህሎት ላይ ያተኮረ የኦንላይን ቢዝነስ ስልጠና እንዲያገኙ ይደረጋል - የአማራ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ

ባሕርዳር፤ ነሐሴ 17/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት ከአምስት ሚሊዮን የሚበልጡ ወጣቶችን በዲጂታል ኢኒሼቲቭ የኦንላይን ቢዝነስ ስልጠና ተጠቃሚ ለማድረግ እንደሚሰራ የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ አስታወቀ።
"በዲጂታል ዕውቀትና ክህሎት የታነፀ ትውልድ ለአሻጋሪና ዘላቂ ዕድገት" በሚል መሪ ሃሳብ የዲጂታል ኢንሼቲቭ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በባሕርዳር ከተማ እየተካሄደ ነው።
በመርሃ ግብሩ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
በማስጀመሪያ መድረኩ ላይ የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ አቤል ፈለቀ እንደገለጹት፤ እስከ 2022 ዓ.ም ከ5 ሚሊዮን በላይ የክልሉን ወጣቶች በዲጂታል ዕውቀትና ክህሎት ላይ ያተኮረ የኦንላይን ቢዝነስ ስልጠና እንዲያገኙ ይደረጋል።
ለዚህም የማመቻቸት ተግባር እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው፤ በሂደቱም በትምህርት ላይ ለውጥ ለማምጣትና የኦን ላይን የስራ ዕድል ፈጠራን ተደራሽ ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል።
የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን የማስፋፋት፣ የፈጠራ ሃሳብና ችግር ፈቺ ትውልድን ለመገንባት እየተሰራ እንደሚገኝም አንስተዋል።
በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የዲጂታሉ ዓለም በፈጠነ የዕድገት ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
ዘመኑን የዋጀ ትውልድ ለመገንባት መምህራን ራሳቸውን ሊያዘጋጁ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
ለዚህም የሚያግዙ ከ9ኛ እስከ 12ኛ ክፍል ተማሪ ተኮር የማስተማሪያ ሞጅሎች እየተዘጋጁ እንደሚገኙም ጠቅሰዋል።
ስልጠናው የኦን ላይን ቢዝነስ ላይ አተኩሮ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ አተኩሮ እንደሚሰጥ ተመልክቷል።