ቀጥታ፡

ለውጭ ገበያ ከቀረቡ የስጋ እና የእርድ ተረፈ ምርቶች 120 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ተገኘ

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 26/2017 (ኢዜአ) :-በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ለውጭ ገበያ ከቀረቡ የስጋ እና የእርድ ተረፈ ምርቶች 120 ሚሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱን የኢፌዲሪ እንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ገለጸ፡፡ 

የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አስራት ጤራ (ዶ/ር) በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የእንስሳት ምርትን በመጨመር  ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ በርካታ ስራዎች መሰራታቸውን ተናግረዋል፡፡


 

ለአብነትም የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል፣ ብቁ ሙያተኞችን ማፍራት፣ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን ጥራት እንዲጠበቅ ማስቻል እና ሌሎች ከተከናወኑ ስራዎች መካከል መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡

ኢትዮጵያ ከስጋ በተጨማሪ 21 የሚጠጉ የእርድ ተረፈ ምርቶች ለውጭ እንደምትልክ ገልጸው ለአብነትም ኩላሊትና ጉበት ተጠቃሽ መሆናቸውን ተናግረዋል።

በዚህም ኢትዮጵያ ከእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች የምታገኘው ገቢ እንዲሻሻል አቅም እየፈጠረ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ 

በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 22ሺህ 620 ቶን የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን ለውጭ ገበያ  በማቅረብ 120 ሚሊየን ዶላር ገቢ ማግኘት መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡


 

ይህም ከባለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር በገቢ 53 በመቶ ብልጫ ያለው መሆኑን  ጠቁመዋል።   

ስጋ እና የስጋ ተረፈ ምርቶች በስፋት ለገበያ ከቀረቡባቸው የዓለም ሀገራት መካከልም ሳኡዲ አረቢያ እና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ያሉበት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የማር እና የሰም ምርቶችን ወደ ጃፓን፣ ጀርመን እና አሜሪካ መላክ መቻሉንም ገልጸዋል፡፡ 

የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን ጥራት ይበልጥ ማስጠበቅ፣ ለእንስሳት ተገቢውን እንክብካቤ ማድረግ ብሎም የገበያ መዳረሻ ቦታዎች ማስፋት በቀጣይ ከሚሰሩ ስራዎች መካከል መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡   


 

ዋና ዳይሬክተሩ አክለውም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሰው ሰራሽ የዝርያዎች ማዳቀል ስራም 1 ሚሊዮን 970 ሺህ ዝርያቸው የተሻሻሉ ጥጆች እንዲወለዱ መደረጉን ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም