ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ኤርትራ በአፋር ህዝብ ላይ እየፈጸመች ያለውን ግፍ የተሞላበት የዘር ማጥፋት ዘመቻ ሊያስቆም ይገባል -  የአፋር ቀይ ባህር ዴሞክራሲያዊ ድርጅት 

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 15/ 2017 (ኢዜአ)፦  ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ኤርትራ በአፋር ህዝብ ላይ እየፈጸመች ያለውን ግፍ የተሞላበት የዘር ማጥፋት ዘመቻ በአስቸኳይ እንዲያስቆም የአፋር ቀይ ባህር ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ጥሪ አቀረበ።

በፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የሚመራው በዳንካሊያ ክልል የሚገኙ የአፋር ህዝቦች የተቀናጀ የዘር ሽብር ዘመቻ መክፈቱን አመልክቷል። 

ድርጅቱ ኤርትራ በአፋር ህዝብ ላይ እየፈጸመ ያለው ያልተቋረጠ የጭካኔ ተግባር የዓለምን አስቸኳይ ትኩረት ይሻል በሚል መግለጫ  አውጥቷል። 

በመግለጫው የኤርትራ መንግስት መጠነ ሰፊ ግድያዎች፣ በግዳጅ ለውትድርና መመልመል፣ አስገድዶ መሰወር፣ ማሰቃየት እና ሆን ብሎ የአፋር ማህበረሰቦችን ማፈናቀል ጨምሮ የተለያዩ ግፎችን እየፈጸመ መሆኑን አመልክቷል። 

ድርጅቱ ኤርትራ የምትፈጽማቸው ድርጊቶች በመንግስት ደረጃ የተቀነባበረ የባህል እና የዘር ማጥፋት ዘመቻ አካል ነው ሲል ገልጿል።  

 

እየፈጸሙ ያሉ በደሎች የአንድ ጊዜ ብቻ ክስተቶች አይደለም ይልቁንም በተጠና ፖሊሲ  አፋርን ከኤርትራ ለማጥፋት በመንግስት እየተፈጸመ ያለ ተግባር ነው ብሏል።

ድርጅቱ ጉዳዩን አስመልክቶ በግንቦት ወር 2017 ዓ.ም ለአፍሪካ የሰብዓዊና የህዝብ መብቶች ኮሚሽን በይፋ አቤቱታ ማቅረቡን ገልጾ በአፍሪካ ቻርተር የተቀመጡ 25 የመብት ጥሰቶችን መፈጸማቸውን አመልክቷል። 

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ የአፍሪካ ህብረት፣ የአውሮፓ ህብረት፣ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) እና ለዔሎች ዓለም አቀፍ ተቋማት በኤርትራ መንግስት ባለስልጣናት እና ተቋማት ማዕቀብ እንዲጥሉ ጥሪ አቅርቧል።


ተቋማቱ ዓለም አቀፍ የሕግ እርምጃ እንዲወስዱ እና የአፋር ህዝብ የፍትህ፣ የመጠበቅ እና በራሱ የመወሰን መብት እውቅና እንዲሰጡ ጠይቋል። 

ኤርትራ በአፋር ህዝብ ላይ እየፈጸመች ያለው ግፍ እና በደል በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ገለልተኛ የሰብዓዊ መብት ባለሙያዎች እና በሰብዓዊ መብት ተቋማት በሰፊው በማስረጃ ተሰንዶ ያለ ጉዳይ መሆኑን አመልክቷል። 

በኤርትራ መንግስት ላይ እርምጃ ካልተወሰደ የዜጎች ህይወት መቀጠፉን እንደሚቀጥል እና ሊቀለበስ የማይችል የባህል ውድመት እንደሚፈጥር ድርጅቱ አስጠንቅቋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም