የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የዲጂታል እውቀትን በማስፋፋት፣ የተቋማት የመፈጸም አቅም ማጎልበትን ዓላማ ያደረገ ነው - ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 11/2017(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የዲጂታል እውቀትን በማስፋፋት፣ የግለሰቦችንና የተቋማትን የመፈጸም አቅም ማጎልበትን ቁልፍ ዓላማ ያደረገ መሆኑን የኢኖቬሸን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር) ገለጹ።

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር "በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ረቂቅ ስትራቴጂ ሰነድ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት እያካሄደ ይገኛል።


 

ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ(ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንዳሉት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 የተገኙ ስኬቶች ላይ ተመስርቶ አዳዲስ የዲጂታል እድገቶች ላይ ትኩረት ያደረገ ነው።

ስትራቴጂው ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ እና የዲጂታል የህዝብ መሰረተ ልማት እስከ ስማርት ከተሞች፣ ድንበር ተሻጋሪ ኢ-ኮሜርስ፣ ዲጂታል ሉዓላዊነት የመሳሰሉ ጽንሰ ሃስቦችን አካቶ የተዘጋጀ ነው ብለዋል።

ስትራቴጂው ቴክኖሎጂን በመጠቀም ስለሚፈጠሩ የስራ እድሎች፣ አካታችና ፍትሃዊ ልማትን እንዲሁም ሁለንተናዊ ብልጽግናን አላማ አድርጎ የተነደፈ መሆኑንም ተናግረዋል።


 

የዲጂታል እውቀትን በማስፋፋትና የተቋም አቅምን በመገንባት የግለሰቦችን እንዲሁም የተቋማትን የመፈጸም አቅም ማጎልበት ከስትራቴጂው ዋና አላማዎች መካከል እንደሆነም ገልጸዋል።

አካታች የዲጂታል ኢኮኖሚ እድገትን ማፋጠን፣ ሁሉን አቀፍ የዲጂታል ተደራሽነትን ማሳደግ እና ኢትዮጵያን ለዲጂታል የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ተመራጭ መዳረሻ ማድረግ ከስትራቴጂው ዓላማዎች መካከል መሆኑንም አክለዋል።

ሀገራዊ ዳታዎችንና አለም አቀፍ የቴክኖሎጂ አዝማሚያዎችን እንዲሁም ሀገራዊ የልማት ፍላጎቶችን መሰረት ያደረጉ መረጃዎችን በማሰባሰብና በመተንተን የዲጂታል ልማቱ ምሰሶዎችንና የትኩረት አቅጣጫዎችን የለየ መሆኑንም ጨምረው አብራርተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም