የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ከመስከረም 2018 ዓ.ም ጀምሮ ይካሔዳል - የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ከመስከረም 2018 ዓ.ም ጀምሮ እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር በከር ሻሌ (ዶ/ር) ገለጹ።

አገልግሎቱ ዛሬ የ2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ የቅድመ-ዝግጅት ተግባራት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር አካሒዷል።


 

በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጀቶች ቆጠራ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት ተገኝተዋል።

በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ስታስቲክስ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር በከር ሻሌ (ዶ/ር) በ2018 ዓ.ም የሚጀመረውን የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ በተመለከተ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

ዋና ዳይሬክተሩ በመግለጫቸው፤ አገልግሎቱ ከ2016 ዓ.ም እስከ 2018 ዓ.ም የስታስቲክስ ልማት ፕሮግራም ቀርጾ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡

ከልማት መርሃ ግብሮቹ መካከል የኢትዮጵያ የስነ ህዝብና ጤና ጥናት፤ የኢትዮጵያ የግብርና ቆጠራ፣ ብሔራዊ የተቀናጀ የቤተሰብ ጥናትና የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ዋና ዋናዎቹ መሆናቸውን ገልጸዋል።

ከነዚህ መካከል የኢትዮጵያ የስነ ህዝብና ጤና ጥናት ማለቁን ጠቁመው፤ የኢትዮጵያ የግብርና ቆጠራ እና ብሔራዊ የተቀናጀ የቤተሰብ ጥናት በመጠናቀቅ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ በመስከረም እንደሚጀመር ገልጸው፤ በቆጠራው በመላው አገሪቷ የሚገኙ ከፍተኛ፣ መካከለኛ እና ዝቅተኛ  ኢንተርፕራይዞች እንደሚካተቱ ተናግረዋል። 

ከቆጠራው የሚገኙ መረጃዎች በዘርፉ ለሚዘጋጁ እቅዶች፣ ፖሊሲዎች እና ስትራቴጂ ትክክለኛ ግብዓት ሆነው እንደሚያገለግሉ ጠቁመዋል፡፡

ስለሆነም በመላው አገሪቷ የሚገኙ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ቆጠራው የሚጀመራው በአዲስ ዓመት መግቢያ መሆኑን ተገንዝበው ከወዲሁ ዝግጅት እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ አስተባባሪ ኮሚቴ የቅድመ ዝግጅት ስራውን ዛሬ በይፋ መጀመሩን ገልጸው፤ ስራው የስነ ጥናት ዘዴውንና ሽፋኑን እንደሚወስንም ነው የተናገሩት።

 
 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም