በክልሉ የግብርና ዘርፉን ምርታማነት በማሳደግ ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገው ጥረት አበረታች ነው - የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴ

ጋምቤላ ፤ሀምሌ 8 /2017 (ኢዜአ) ፡-በጋምቤላ ክልል የግብርና ዘርፉን ምርታማነት በማሳደግ ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገው ጥረት አበረታች መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት ገለፁ። 

‎በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት በጋምቤላ ክልል ያለውን ወቅታዊ የግብርና ልማት እንቅስቃሴ ተመልክተዋል። 


 

ከጉብኝቱ በኋላ ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡት የቋሚ ኮሚቴው አባላት ቡድን መሪ ወይዘሮ ሉባባ ሰይድ፤ መንግስት ለግብርናው ዘርፍ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ምርትና ምርታማነት የማሳደግ ጥረቱን አጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። 

በግብርና ዘርፍ ብዝሃ የምርት አማራጮችን ከማስፋት ባለፈ የግብዓት አቅርቦትን በማሟላት ምርታማነት እንዲያድግ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።


 

በዘርፉ ልማት የጋምቤላ ክልል እምቅ አቅም ያለው በመሆኑ ልማቱን በማሳለጥ እንደ ሀገር ከተረጂነት ለመላቀቅ ለተያዘው እቅድ ትልቅ አቅም ይሆናል ሲሉም አንስተዋል። 

በመሆኑም በጋምቤላ ክልል የግብርና ዘርፉን ምርታማነት በማሳደግ ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገው ጥረት ተስፋ የታየበት ነው ብለዋል።


 

የቋሚ ኮሚቴው አባል ወይዘሮ እታገኝ እሸቱ፤ በበኩላቸው በክልሉ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመላቀቅ እየተከናወነ ያለው ተግባር የሚበረታታ መሆኑን ተናግረዋል።

በክልሉ ያሉ እምቅ ፀጋዎችን በአግባቡ ማልማት ከተቻለ ለሀገር የሚተርፍ ሃብት ያለበት መሆኑን በመስክ ምልከታችን አረጋግጠናል ሲሉም ገልጸዋል።


 

የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዳግም ምላሺን፤ በዘንድሮው መኸር ከ172 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ስለመሸፈኑ አንስተው የተሻለ ምርት እንዲገኝ ቅንጅታዊ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። 

በምርት ዘመኑ በዘር ከተሸፈነው የእርሻ መሬት ከ5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ እቅድ መያዙንም ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም