ኢትዮጵያ የዲጂታል ውህደት ዕድገትን እያስመዘገበች ነው 

አዲስ አበባ፣ሐምሌ 8/2017 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የዲጂታል ውህደት ዕድገትን  እያስመዘገበች ነው ሲሉ የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ።

25ኛው የአፍሪካ ቀንድ ኢኒሼቲቭ የፋይናንስ ሚኒስትሮች ስብሰባ በኬኒያ ናይሮቢ ተካሂዷል፡፡

በመድረኩ የተሳተፉት ሚኒስትር ዴኤታው ኢትዮጵያ የዲጂታል ውህደት በመፍጠር በኩል  ጠንካራ የዲጂታል ግስጋሴ ላይ መሆኗን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዲጅታል ግስጋሴ  ከአፍሪካ ቀንድ የዲጂታል ፖሊሲ ማትሪክስ ጋር የተጣጣመ መሆኑን ጠቁመዋል።

የአፍሪካ ቀንድ ዲጅታል ውህደትን እውን  ከማድረግ አንጻር  ሀገራቱ ጥሩ አፈጻጸም እያስመዘገቡ ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ኢትዮጵያ የተሻለ አፈፃፀም ካላቸው መካከል አንዷ  መሆኗን ነው የገለጹት፡፡

ኢትዮጵያ ያደረገችው ሪፎርም የቴሌኮም ዘርፎችን ነፃ ማድረግ፣የግል መረጃ ጥበቃ እና የሳይበር ደህንነት ህጎችን ማውጣት፣የፋይበር መሠረተ ልማትን ማስፋፋት መቻሉን ገልጸዋል።

 እንዲሁም  ከ19 ሚሊዮን በላይ ዜጎች በዲጂታል መታወቂያ ስርዓት መመዝገባቸውን ጠቅሰዋል።

አክለውም፥ ከ54 ሚሊዮን በላይ የቴሌብር ተጠቃሚዎች መኖራቸውን እና 4.6 ትሪሊዮን ብር የግብይት መጠን መፈጸሙ ኢትዮጵያ በፋይናንሺያል አካታችነት ያላትን ተነሳሽነት ያሳያል ብለዋል። 

የቀጣናውን የሀይል ትስስር አስፈላጊነት ገልጸው፥አጋር አካላት ለሚያደርጉት ቀጣይነት ያለው ድጋፍ አመስግነዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም