ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 4ሺህ 700 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ ገብቷል - ቢሮው - ኢዜአ አማርኛ
ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 4ሺህ 700 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ ገብቷል - ቢሮው

አሶሳ፤ ሐምሌ 7/2017(ኢዜአ)፦ ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 4ሺህ 700 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ መግባቱን የክልሉ ማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ።
የቢሮው ኃላፊ አድማሱ ሞርካ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደተናገሩት በ2017 በጀት ዓመት 1ሺህ 500 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ ለማስገባት ታቅዶ ሲሰራ ቆይቷል።
በቅንጅት በተከናወኑ ተግባራት ከዕቅዱ በላይ 4ሺህ 700 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ ገቢ መደረጉን ገልጸዋል።
ከዕቅዱ በላይ የተከናወነበት ምክንያትም መንግስት ለወርቅ አቅራቢዎች ያደረገው ማበረታቻ እና ህገ-ወጥ ግብይት መቀነስ ትልቅ አስተዋፅኦ ነበራቸው ብለዋል።
በተለይም በሀገር አቀፍ ደረጃ በተተገበረው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ዘርፉ እንዲነቃቃና አምራቹ ተጠቃሚ እንዲሆን ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ጠቅሰዋል።
በክልሉ የተመረተው ወርቅ በአነስተኛና ባህላዊ ወርቅ አምራቾች መሆኑን ገልጸው፤ ይህም የህብረተሰቡን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት አሳድጓል ነው ያሉት።
ከወርቅ በተጨማሪ የድንጋይ ከሰልና እምነበረድ በስፋት እየተመረተ መሆኑን ጠቅሰው በክልሉ የሚገኙ የማዕድን ሀብቶች ጥቅም ላይ እንዲውሉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል።
ከማዕድን ምርቱ 49 ሚሊዮን ብር መሰበሰቡንም ነው አቶ አድማሱ ጨምረው የተናገሩት።
በቀጣይ ትላልቅ ካምፓኒዎችን በመጋበዝ በክልሉ በማዕድን ዘርፍ ለማሰማራት ዝግጅት መጠናቀቁንም አስታውቀዋል።