ዓለም አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራቾች በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎት እያሳዩ ነው

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራችና ሻጭ ድርጅቶች በኢትዮጵያ ምርታቸውን ለማቅረብና በዘርፉ በኢንቨስትመንት ለመሰማራት ፍላጎት እያሳዩ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን ገለፁ።

በየዓመቱ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን የሚገጣጥሙና ለሽያጭ የሚያቀርቡ ተቋማት ቁጥር እያደገ መምጣቱንም ገልፀዋል።

የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን ለኢዜአ እንደገለጹት በአገሪቱ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለማስፋፋትና በዘርፉ ያለውን ኢንቨስትመንት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው።


 

የነዳጅ ኃይል ጥገኝነት ለመቀነስና የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ዘርፉን አገሪቱ ካላት እምቅ የታዳሽ ሃይል ሀብት ተጠቃሚ ለማድረግ  አበረታች ስራዎች መጀመራቸውን ተናግረዋል።

ሀገር አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከሪካሪዎች ስትራቴጂን ተግባር ላይ በማዋል ተግባራዊነቱን ለማፋጠንና ኢንቨስትመንቱን ሳቢ ለማድረግ የሚረዱ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። 

መንግስት በነዳጅ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክትሪክ የመቀየር እንዲሁም የነዳጅ አጠቃቀምንና ብክለትን በሚቀንሱ ቴክኖሎጂዎች ላይ የሚሰሩ ስራዎችን እያበረታታ መሆኑንም አስታውቀዋል።

በነዳጅ የሚሰሩ የቤት አውቶሞቢሎች ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ እገዳ መጣሉን አንስተው በአለም ገበያ ተደራሽ ያልሆኑ ከባድ ተሽከርካሪዎችና መሳሪያዎች በእገዳው አለመካተታቸውን ጠቅሰዋል።

በቅርቡ ከሁለት እግር ጀምሮ እስከ ከተማ አውቶብስ ያሉና በነዳጅ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን በሀገር ውስጥ መገጣጠም መከልከሉን አንስተዋል። 


 

በዘርፉ ለተሰማሩ ባለሃብቶች የተለያዩ ማበረታቻዎች በፖሊሲ፣ ስትራቴጂና በመመሪያ ተደግፈው  ተግባራዊ በመደረጋቸው በርካታ ውጤት ተገኝቷል ብለዋል።

በአሁኑ ወቅት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቁጥር ከ115 ሺህ በላይ እንዲሁም የኤሌክትሪክ ተሽከሪካሪ መገጣጠሚያ ድርጅቶች ቁጥር ከ15 በላይ መድረሱን በማሳያነት ጠቅሰዋል።

ኢትዮጵያ ለዘርፉ የሰጠችውን ትኩረት ተከትሎ አሁን ላይ በርካታ ዓለም አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራቾችና ሻጮች በዘርፉ በኢንቨስትመንት ለመሰማራት ሰፊ ፍላጎት እያሳዩ መሆኑንም ጠቅሰዋል።

በአሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የሚሰጥ የከተማ የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎትን ለማስፋፋት የሚረዱ ስራዎች በመንግስትና በግል አጋርነት መጀመራቸውን ጠቅሰዋል።

በአዲስ አበባ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ባትሪ መሙያ ቋሚ ጣቢያዎች ቁጥር ከ90 እንደማይበልጥ አንስተው ይህንን ለማሳደግ የመንግስት የልማት ድርጅቶችና የግል ባለሀብቶች በዘርፉ እንዲሰማሩ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም