በሀገር ደረጃ የተቀመጡ ራእዮች እና ግቦች እውን እንዲሆኑ የሚያስችሉ የምርምር ውጤቶች ተደራሽ እየተደረጉ ነው - የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦ በሀገር  ደረጃ የተቀመጡ ራእዮች እና ግቦች እውን እንዲሆኑ የሚያስችሉ የምርምር ውጤቶች ተደራሽ እየተደረጉ መሆኑን የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ ጸጋ ገለጹ።

ባለፉት የለውጥ አመታት 280 የሚሆኑ የምርምር ስራዎች መከናወናቸውን ጠቁመዋል።

ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ ጸጋ ኢንስቲትዩቱ በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ጥናት የሚያደርግ ተቋም ነው ብለዋል።

በዚህም 52 የትኩረት መስኮችን በመለየት በ14 ዲፓርትመንቶች 6 ማእከሎችን በማዘጋጀት እየሰራ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።

የምርምር ስራዎቹም በማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ላይ ያተኮሩ መሆናቸውን አመላክተዋል።

ማስረጃን መሰረት ያደረጉ የጥናት ውጤቶችንም ለሚመለከታቸው ፖሊሲ አውጪዎች እና አስፈጻሚዎች ተደራሽ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

ባለፉት የለውጥ አመታት 280 የሚሆኑ ምርምሮች መደረጋቸውን ተናግረዋል።

እነዚህ ምርምሮችም ነባር ፖሊሲዎችን የፈተሹ፣ አዳዲስ ፖሊሲዎችን ያመላከቱ እና ፋይዳ ምልከታ ላይ ያተኮሩ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

የጥናት መነሻዎቹ እንደ ሀገር የተቀመጡ እቅዶች እና የመንግስት አቅጣጫዎች መሆናቸውን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ ፈጣን እደገት ያስመዘገቡ ሀገራት ትልልቅ የምርምር ተቋማት እንዳላቸው አንስተዋል።

እንደ ሀገር የተቀመጡ ግቦች እና ህልሞች እውን እንዲሆኑ በጥናት መደገፍ እንደሚገባ በመግለጽ።

ኢንስቲትዩቱ በዚህ ረገድ የተሰጠውን ተልእኮ በመውሰድ ሁለንተናዊ ብልጽግናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ጥናቶችን በማጥናት ተደራሽ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

በተለዩ የትኩረት መስኮች ላይ ፖሊሲዎች ከመነደፋቸው በፊት የምርምር ስራዎች እንደሚሰሩ አንስተው፤ ተፈጻሚ ከሆኑ በኋላም ምን አይነት ውጤት አመጣ የሚለው እየተሰራበት መሆኑን ገልጸዋል።

ለአንድ ሀገር እድገት ችግር ፈቺ የምርምር ውጤቶች አስፈላጊ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ኢንስቲትዩቱም እንደ ሀገር የተቀመጡ ራእዮች እና ግቦች እውን እንዲሆኑ የሚያስችሉ የምርምር ውጤቶችን ተደራሽ እያደረገ መሆኑን አመላክተዋል።

በዚህ አመትም በኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ 35 ጥናቶች መጠናታቸውን ተናግረዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም