የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ወጪን በራስ አቅም የመሸፈን ሂደቱን አሳድጓል

አሶሳ፤ ሐምሌ 6/2017 (ኢዜአ)፦በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በ2017 በጀት ዓመት በቅንጅት በተሰበሰበ ገቢ ወጪን በራስ የመሸፈን ሂደቱን በማሳደግ ላይ መሆኑን የክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን አስታወቀ። 

የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ተፈሪ አበበ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ በበጀት ዓመቱ 4 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ዕቅድ ተይዞ ሲሰራ ቆይቷል።

በበጀት ዓመቱን በተቀናጀ አኳኋን በተሰራው ሥራም ከእቅድ በላይ አምስት ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ተችሏል ብለዋል።

ከተለያዩ ተቋማት ጋር የነበረው ቅንጅታዊ አሰራር መጠናከር፣ ዘመናዊ የታክስ አስተዳደር ስርዓት መስፈን እና የህግ አሰራሮች ላይ ማሻሻያ መደረጉ የላቀ አፈጻጸም እንዲመዘገብ አድርጓል ብለዋል።

ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ46 በመቶ ብልጫ እንዳለው አቶ ተፈሪ አስታውቀዋል።

ክልሉ የራሱን ወጪ የመሸፈን አቅሙን ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው በዚህ ዓመት የራሱን ወጪ የመሸፈን አቅሙ ወደ 60 በመቶ ከፍ ማለቱን ተናግረዋል።

ግብር ከፋዩ ግብርን በወቅቱ የመክፈል እና የግብርን አስፈላጊነት እየተገነዘበ በመሆኑ የታክስ ማጭበርበር እና ስወራ እየቀነሰ መምጣቱን አመላክተዋል።

ክልሉ ካለው የገቢ አማራጭ አንፃር መሰብሰብ የሚገባውን ገቢ አላገኘም ያሉት አቶ ተፈሪ ተጨማሪ የገቢ አማራጮች ላይ ጥናት እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም