በድሬዳዋ አስተዳደር የሚሰበሰብ ገቢ መጨመር የህዝብን የልማት ጥያቄ በራስ ገቢ የመመለስ አቅምን አሳድጎታል

ድሬዳዋ፣ ሐምሌ 5/2017 (ኢዜአ)፡-በድሬዳዋ አስተዳደር የሚሰበሰበው ገቢ እየጨመረ መምጣት የህዝብን የልማት ጥያቄ በራስ ገቢ የመመለስ አቅምን ከ70 በመቶ በላይ ማድረሱን የአስተዳደሩ ገቢዎች ባለስልጣን አስታወቀ። 

የድሬዳዋ ገቢዎች ባለስልጣን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ5 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡም ተገልጿል።

የድሬዳዋ አስተዳደር ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ አብዱልሰላም መሐመድ የተጠናቀቀው በጀት ዓመት የገቢ አሰባሰብና ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ ላይ ዛሬ መግለጫ ሰጥተዋል።

ዋና ዳይሬክተሩ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ አገራዊ ለውጡን ተከትሎ በድሬዳዋ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ሃብት የሚስተካከል ገቢ ለመሰብሰብ በተሰራው ሥራ አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል።

ከሀገራዊ ለውጡ በፊት በአስተዳደሩ የነበረውን ዓመታዊ ገቢ 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር እንደነበር አስታውሰው፣ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ መሰረታዊ ሪፎርም በመካሄዱና ዲጂታል አሠራሮች በመዘርጋታቸው ገቢው በየዓመቱ በቢሊዮን ብሮች ጨምሯል ብለዋል።

ለአብነት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከመንግስትና ከማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶች 6 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ከ5 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ተችሏል ብለዋል።

በእዚህም የዕቅዱን 86 በመቶ ማሳካት መቻሉን ጠቅሰው የዘንድሮ ገቢ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ1 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር በላይ ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል።

በአስተዳደሩ የሚሰበሰበው ገቢ እየጨመረ መምጣት የህዝብን የልማት ጥያቄዎች በራስ ገቢ የመመለስ አቅምን በማሳደግ ከ70 በመቶ በላይ ማድረሱንም አቶ አብዱልሰላም አስታውቀዋል።

ይህም ቢሆን እያደገ የመጣውን የነዋሪውን የልማት ጥያቄዎች በአግባቡ ለመመለስ ገቢን አሟጦ የመሰብሰብ ሥራ በቀጣይም ትኩረት ተሰጥቶት እንደሚከናወን አቶ አብዱልሰላም ገልጸዋል።

በቀጣይም በተለይ በዘርፉ የሚስተዋሉ ብልሹ አሠራሮችን በማረም፣ ዘመናዊ የግብር አሰባሰብ ስርአትን በመተግበርና ያለ ደረሰኝ የሚፈፀም ግብይትን በመከላከል የተሻለ ገቢ ለመሰብሰብ ይሰራል ብለዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም