በመዲናዋ ቀልጣፋ የፍትሕ አገልግሎትን ተደራሽ የማድረግ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ከንቲባ አዳነች አቤቤ - ኢዜአ አማርኛ
በመዲናዋ ቀልጣፋ የፍትሕ አገልግሎትን ተደራሽ የማድረግ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ከንቲባ አዳነች አቤቤ

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ በመዲናዋ ቀልጣፋ የፍትሕ አገልግሎትን ለህብረተሰቡ ተደራሽ የማድረግ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር 4ኛ መደበኛ ጉባኤውን የተለያዩ ውሳኔዎችና ሹመቶችን በማጽደቅ ተጠናቋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአዲስ አበባ ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤቶች ፕሬዝዳንት ተስፋዬ መለሰ የፍርድ ቤቶችን የ2017 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ለምክር ቤቱ አቅርበዋል።
በበጀት ዓመቱ ፍርድ ቤቶች ለሚቀርቡላቸው ጉዳዮች ቀልጣፋ፣ ውጤታማና ተደራሽ የዳኝነት አገልግሎት ለመስጠት ስራዎች ተሰርተዋል ብለዋል።
የፍርድ ቤት የአገልግሎት ቅልጥፍና መለኪያዎች የመዛግብት ማጣራት ምጣኔና በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ውሳኔ መስጠት መሆኑን በሪፖርታቸው አመላክተዋል።
በ2017 በጀት ዓመት የመዛግብት የማጣራት ምጣኔን 97 በመቶ ለማድረስ ታቅዶ በሁሉም ፍርድ ቤቶች መሰራቱን አብራርተዋል።
ከ2016 በጀት ዓመት የዞሩና በ2017 አዲስ የተከፈቱትን ጨምሮ ከአጠቃላይ 162ሺህ 97 መዛግብት ውስጥ 159 ሺህ 65ቱ እልባት አግኝተዋል ብለዋል።
ዓመታዊ የመዛግብት የማጣራት ምጣኔውም 98 በመቶ መፈጸሙን ነው ያነሱት።
የዳኝነት ውጤታማነትን ለማረጋገጥ ዳኞች ስራቸውን ሲያከናውኑ ከፈጻሚው አካል፣ ከፍርድ ቤት አመራሮችና ከጎንዮሽ ተጽእኖ ነጻና ገለልተኛ ሆነው እንዲያገለግሉ እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።
በፍርድ ቤቶች የአገልግሎት አሰጣጥን የበለጠ ውጤታማ ለማድረግና የተገልጋይ እርካታን ለመጨመር የተለያዩ የሪፎርም ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ አብራርተዋል።
የፍርድ ቤት አገልግሎትን በቴክኖሎጂ መደገፍ፣ ቀልጣፋና ተደራሽ አገልግሎት መስጠት ብልሹ ስነ-ምግባር የታየባቸው ሰራተኞችና ዳኞች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ፍርድ ቤቶችን ማጠናከር የዜጎችን መብት ለማስጠበቅና ህጎችን በትክክል በመተግበር የፍትሕ አገልግሎት ውጤታማነትን ለመጨመር ያግዛል ብለዋል።
ልማትን ለማፋጠን፣ የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥና ፍትሃዊነት ለማስፈን በፍርድ ቤቶች የተጀመሩ ሪፎርሞችን ማጠናከር እንደሚገባም ነው አፅንኦት የሰጡት።
ከተማ አስተዳደሩም ለፍርድ ቤቶች አስፈላጊውን መሰረተ ልማት በማሟላት ግልጽ እና ቀልጣፋ የፍትህ አገልግሎትን እውን ለማድረግ ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ከንቲባዋ አረጋግጠዋል።
የምክር ቤት አባላት በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች የ2017 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ላይ ያነሷቸው አስተያየቶች በግብዓትነት በመውሰድና ለጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ሪፖርቱ ጸድቋል።