በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ለገጠር መንገድ ተደራሽነት ትኩረት ተሰጥቷል - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ

ወላይታ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ብልጽግናን እውን ለማድረግ ለገጠር መንገድ ተደራሽነት ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ።

ርዕሰ መስተዳድሩ በወላይታ ዞን ዳሞት ጋሌ ወረዳ ከ36 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነባውን 20 ኪሎ ሜትር የገጠር ተደራሽ መንገድ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።


 

በዚህ ወቅት ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት ገጠርን ከከተማ የሚያገናኝ መንገድ መገንባት አርሶ አደሩ የግብርና ምርቱን ለገበያ ለማቅረብና የፋብሪካ ሸቀጦችን በቀላሉ ወደ አካባቢው ማስግባት የሚያስችለው ነው።

ይህም የአርሶ አደሩን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ያሳድጋል ያሉት አቶ ጥላሁን፣ የክልሉ መንግስት የህዝብን የመንገድ ተደራሽነት ጥያቄ ለመፍታት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን አመልክትዋል።

ዛሬ የተመረቀው መንገድ ለእዚህ አንድ ማሳያ መሆኑን ገልጸው፣ ህብረተሰቡ የተገነቡ መንገዶች ለረጅም ጊዜ አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ መጠበቅ እንዳለበትም አሳስበዋል።


 

የመንገዶቹ መገንባት የአርሶ አደሮችን ማህበራዊ ግንኙነት እንደሚያቀላጥፍ የገለጹት ደግሞ የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ ናቸው።

የመንገዶቹ መጠናቀቅ የግብርና ውጤቶችን በቀላሉ ወደ ከተማ ለመውሰድ እንዲሁም ነፍሰጡሮችን ጨምሮ ህሙማንን ወደ ጤና ተቋማት በፍጥነት ለማድረስ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል።

የመንገዶቹ ግንባታ በታለመለት የጊዜ ገደብ ውስጥ እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላደረጉ ባለድርሻ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።

መንገዱ ከቦዲቲ ከተማ ተነስቶ ቦሎሶ ሶሬ ወረዳን በማቋረጥ ወደ ወላይታ ሶዶ ከተማ ከሚወስድ የአስፖልት መንገድ ጋር እንደሚያገናኝ ተገልጿል።

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ርዕሰ መስተደድር ጥላሁን ከበደ፣ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) እንዲሁም የክልልና የዞን ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም