የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቪየትናም ዋና ከተማ ሃኖይ አዲስ የመንገደኞች በረራ ጀመረ - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቪየትናም ዋና ከተማ ሃኖይ አዲስ የመንገደኞች በረራ ጀመረ

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቪየትናም ዋና ከተማ ሃኖይ አዲስ የመንገደኞች በረራ ጀምሯል።
በማስጀመሪያ መርሀግብሩ የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ደንጌ ቦሩ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው የአየር መንገዱ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች የቪየትናም የንግድ ተቋማት ተወካዮች ታድመዋል።
አየር መንገዱ በሳምንት አራት ጊዜ የመንገደኞች በረራ የሚያደርግ መሆኑ ተገልጿል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው በዚሁ ወቅት እንዳሉት በረራው የሀገራቱን ግንኙነት የሚያጎለብት ነው።
ይህ አዲስ መስመር በኢትዮጵያ እና ቪየትናም መካከል ያለውን የንግድ፣ ቱሪዝም እና የባህል ልውውጥ የሚያሳድግ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
እንዲሁም በአፍሪካ እና በደቡብ ምሥራቅ እስያ መካከል ቀጥተኛ ትስስር እንዲኖር በማድረግ የኢትዮጵያ አየር መንገድን ስትራቴጂካዊ መስፋፋት በማጠናከር ዓለም አቀፍ ግንኙነትን የሚያጎለብት መሆኑን ተናግረዋል።
የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ደንጌ ቦሩ፥ አየር መንገዱ የስኬት ማሳያ የሆነ ተቋም መሆኑን ገልጸዋል።
አየር መንገዱ እንደ ሀገር የተያዙ ኢኮኖሚያዊ እቅዶች እንዲሳኩ የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አንስተዋል።
በረራው የሀገራቱን ግንኙነት በጉልህ የሚያሳድግ መሆኑን ተናግረዋል።
በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመካከለኛው ምስራቅ እስያ እና ፓስፊክ ሀገራት ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራል ደዋኖ ከድር በበኩላቸው አየር መንገዱ ለዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ገልጸዋል።
በሁለቱ ሀገራት መካከል የተጀመረው በረራ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ጠቀሜታ እንዳለው አመላክተዋል።