በምስራቅ ቦረና ዞን ከ4 ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የተገነቡ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቁ - ኢዜአ አማርኛ
በምስራቅ ቦረና ዞን ከ4 ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የተገነቡ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቁ

ነገሌ ቦረና፤ ሰኔ 30/2017 (ኢዜአ)፡- በምስራቅ ቦረና ዞን ከ4 ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት መብቃታቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ።
በምክትል ፕሬዚዳንት ማዕረግ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ ሳዳት ነሻ ዛሬ በነገሌ ቦረና ከተማ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን መርቀዋል፡፡
በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱረዛቅ ሁሴን እንደገለጹት፤ ለአገልግሎት ከበቁት ውስጥ የመጠጥ ውሀ፣ የጤና፣ የትምህርትና የመንገድ መሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ይገኙበታል።
የመንግስት ድጋፍና የሕዝቡ ተሳትፎን ጨምሮ የተገነቡት እነዚህ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ከ4 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደተደረገባቸው አስታውቀዋል።
ፕሮጀክቶቹ ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸው የሕብረተሰቡን የመሰረተ ልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄን ደረጃ በደረጃ ምላሽ ለመስጠት የተደረገው ጥረት አካል እንደሆኑ አስረድተዋል፡፡
ለፕሮጀክቶቹ ግንባታ መሳካት ሕዝቡ ፣ የፌዴራልና የክልሉ መንግስት ላበረከቱት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ምስጋና አቅርበዋል፡፡
በምክትል ፕሬዚዳንት ማዕረግ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ ሳዳት ነሻ ፤ የክልሉ መንግስት የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ ከ200 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች እንዳስገነባ ገልጸዋል፡፡
በምስራቅ ቦረና ዞን የተገነቡት ችግር ፈቺ ፕሮጀክቶች የግንባታ አፈጻጸም ልምድና ተሞክሮ የሚወሰድበት ነው ብለዋል፡፡
መንግስት የአርብቶ አደሩን ፍትሀዊ የልማት ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማሳደግ የጀመረው ድጋፍና ትብብር ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡
የዞኑ ሕዝብ የአካባቢውን ሰላምንና የተገነቡ ፕሮጀክቶች በመጠበቅና በመንከባከብ የድርሻውን እንዲወጣም መልዕከት አስተላልፈዋል።