በክልሉ ከተረጂነት ለመላቀቅ የተጀመሩ ውጤታማ ተግባራትን ለማስቀጠል በትጋት ይሰራል - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ ከተረጂነት ለመላቀቅ የተጀመሩ ውጤታማ ተግባራትን ለማስቀጠል በትጋት ይሰራል

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 29/2017(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ከተረጂነት ለመላቀቅ የተጀመሩ ውጤታማ ተግባራትን ለማስቀጠል በትጋት እንደሚሰራ የኦሮሚያ ክልል ኮሙኒኬሽን ቢሮ ሀላፊ ኃይሉ አዱኛ ገለጹ።
የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ እና የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች ባለፉት አምስት ቀናት በደቡብ ኦሮሚያ በሚገኙ አምስት ዞኖች ያደረጉት ጉብኝት ስኬታማ መሆኑ ተገልጿል።
የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ሀላፊ ሀይሉ አዱኛ ጉብኝቱን አስመልክተው በሰጡት ማብራሪያ ጉብኝቱ የልማት ስራዎችን ውጤታማነት ያረጋገጠ ብሎም የቀበሌ አደረጃጀቶች ለህዝቡ እየሰጡ የሚገኙትን የአገልግሎቶች አሰጣጥ የቃኘ መሆኑንና የታለመለትን ግብ ያሳካ ነው ብለዋል።
በክልሉ ፕሬዚዳንት የተመራ ቡድን በቦረና፣ በምዕራብ ጉጂ፣ በምስራቅ ቦረና፣ በጉጂ እና በባሌ ዞኖች የመስክ ምልከታ ማድረጉን ገልጸዋል።
በዚህም ከተረጂነት ለመላቀቅ ምርታማነትን ለማሳደግ የተያዙ ግቦችን አፈጻጸም በመመልከት ውጤታማ ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ አቅጣጫ የተሰጠበት መሆኑን አንስተዋል።
በተለይም በቦረና፣ በምዕራብ ጉጂ፣ በምስራቅ ቦረና እና በጉጂ ቆላማ አካባቢዎች ለዘመናት ያልለሙ መሬቶችን በማልማት ለውጥ መምጣት መጀመሩን ገልጸዋል።
በዚህም የስንዴ ምርትን ጨምሮ ሌሎች የሰብል ዓይነቶችን በክላስተር በማምረት ከተረጂነት ለመላቀቅ የተጀመሩ ስራዎችን ውጤታማነት በማረጋገጥ ላይ እንደሚገኙ ጠቁመው፤ ለቀጣይነቱም በትጋት ይሰራል ብለዋል።
ለዚህም በክልሉ መንግስት እየተገነቡ የሚገኙ የፊና የመስኖ ግድብ ፕሮጀክቶች አጋዥ መሆናቸውን በማከል።
በሌላ መልኩ በክልሉ መንግስት ተደራጅቶ ወደ ስራ የገባው የቀበሌ አደረጃጀት ለሕዝቡ በቅርበት አገልግሎት እየሰጠ መሆኑ የተረጋገጠበት ጉብኝት ነው ብለዋል።
በዚህም አደረጃጀቱ የሕዝቡን የመልካም አስተዳደር እና የልማት ጥያቄዎች በመፍታት ላይ እንደሚገኝ ታይቷል ብለዋል።
በአጠቃላይ ፕሬዚዳንቱ እና የስራ ሃላፊዎች ያደረጉት ጉብኝት ውጤታማ መሆኑን ጠቁመዋል።