በክልሉ ግብርናን በማዘመን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የባለሃብቶች ተሳትፎ ሊጠናከር ይገባል - ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ ግብርናን በማዘመን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የባለሃብቶች ተሳትፎ ሊጠናከር ይገባል - ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ

ጋምቤላ፤ ሰኔ 29/2017(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል ግብርናውን በማዘመን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የባለሃብቶች ተሳትፎ ሊጠናከር እንደሚገባ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ።
ርዕሰ መስተዳድሯ በጋምቤላና አበቦ ወረዳዎች ከዘርፍ አመራሮች ጋር በመሆን በባለሃብቶች የለማ የእርሻ ማሳ ዛሬ ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።
ርዕሰ መስተዳድሯ በጉብኝቱ ወቅት ለኢዜአ እንደገለጹት ለአንድ ሀገር ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት የኢንቨስትመንት ዘርፍ ዋነኛ ድርሻ አለው።
ባለሀብቶች ባሉት ሰፊ የኢንቨስትመንት አማራጮች በመሰማራት ለክልሉ ልማትና አድገት ተሳትፏቸውን ሊያጠናክሩ እንደሚገባ ተናግረዋል።
በክልሉ በተለይም የግብርናውን ልማት በማዘመን የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ለተጀመረው ጥረት በዘርፉ የተሰማሩ ባለሃብቶች አርሶ አደሩን በቴክኖሎጂ በመደገፍ በኩል የበኩላቸውን ሚና ሊወጡ እንደሚገባ ገልጸዋል።
በክልሉ የተፈጠረውን ሰላም በመጠቀም ባለሃብቶች በግርናው ዘርፍ እያከናወኑ ያለው ስራ በእጅጉ የሚደነቅ መሆኑን ገልጸው ሌሎች ባለሃብቶች ወደ ክልሉ በመምጣት በተመሳሳይ ልማት ላይ እንዲሰማሩ ጥሪ አቅርበዋል።
የክልሉ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሎው ኡቡፕ(ዶ/ር) በክልሉ አስተማማኝ ሰላም በመፈጠሩ በተለያዩ የኢንቨስትመንት አማራጮች ለመሰማራት ወደ አካባቢው የሚመጡ ባለሃብቶች ፍሰት እየጨመረ መምጣቱን ተናግረዋል።
በተለይም በግብርናው ዘርፍ ፍቃድ የወሰዱ ባለሃብቶች በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከመቸውም ጊዜ በተለየ ሁኔታ ወደ ልማት በመግባት ውጤታማ ሰራዎችን እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።
የእርሻ ማሳቸውን ካስጎበኙ ባለሃብቶች መካከል አቶ ፍቅሩ ገብረመድን በሰጡት አስተያየት በክልሉ በተለይም በግብርናው ዘርፍ መሰማራታቸውን ተናግረዋል።
የክልሉ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን በሁሉም ዘርፍ አስፈለጊውን ድጋፍና አገዛ እያደረገላቸው መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል።