የመስኖ ፕሮጀክቱ ከዝናብ ጥገኝነት በመላቀቅ ምርታማነትን ለማሳደግ ያስችለናል - የምሥራቅ ቦረና ዞን አርሶ አደሮች

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 28/2017(ኢዜአ)፦የመስኖ ፕሮጀክቱ ከዝናብ ጥገኝነት በመላቀቅ ምርታማነትን ለማሳደግ እንደሚያስችላቸው የምሥራቅ ቦረና ዞን አርሶ አደሮች ተናገሩ። 

በኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ የተመራ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች ቡድን በምስራቅ ቦረና ዞን እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎችን እየጎበኘ ነው። 

እስካሁንም በምስራቅ ቦረና ዞን ጎሮዶላ ወረዳ የተገነባውን የፊና የመስኖ ግድብ ፕሮጀክት፣ የቀበሌ አደረጃጀትን እና የጤና ክላስተርን ጎብኝተዋል። 


 

የክልሉ መንግሥት ሕብረተሰቡን ከዝናብ ጠባቂነት ለማላቀቅ የተለያዩ አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በመሥራት ተጠቃሚነትን በማሳደግ ላይ ይገኛል። 

በዚህም "ፊና" በሚል ከተገነቡ አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች መካከል በምስራቅ ቦረና ዞን ጎሮ ዶላ ወረዳ ተገንብቶ የተጠናቀቀው ፕሮጀክት አንዱ ነው። 

በክልሉ ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ የተመራ የስራ ሃላፊዎች ቡድንም ይህንን የመስኖ ፕሮጀክት ጎብኝቷል። 


 

በዚሁ ወቅት ኢዜአ ያነጋገራቸው አርሶ አደሮች መንግስት በአካባቢው የመስኖ ፕሮጀክት በማስገንባት ለአገልግሎት ዝግጁ ማድረጉን ተናግረዋል። 

አርሶ አደር በቀለ ሚኤቻ እና ከነዩ ውዴሳ እንዳሉትም የመስኖ ፕሮጀክቱ ከዝናብ ጥገኝነት በመላቀቅ ምርታማነትን ለማሳደግ እንደሚረዳቸው ገልጸዋል። 


 

በቀጣይም የግድቡን ውሃ ተጠቅመው አትክልትና ፍራፍሬዎችን ጨምሮ የተለያዩ ሰብሎችን ለማምረት እንደሚጠቀሙበት ተናግረዋል። 


 

በምስራቅ ቦረና ዞን እየተካሄደ በሚገኘው የልማት ስራዎች ጉብኝት የክልሉ ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳን ጨምሮ በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ከፍያለው ተፈራ እንዲሁም ሌሎች የክልሉ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም