በክልሉ ለድህነት ቅነሳ ተግባራትና ለሥራ ዕድል ፈጠራ ትኩረት ይሰጣል-ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ

ሀዋሳ፤ ሰኔ 26/2017 (ኢዜአ)፦በሲዳማ ክልል በድህነት ቅነሳ ተግባራት ላይ በማተኮር ገበያን ማረጋጋትና የሥራ ዕድል መፍጠር ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ ገለጹ፡፡

ክልሉ የተመሰረተበትን 5ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት የውይይት መድረክ በሀዋሳ ከተማ ተካሂዷል፡፡


 

የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ ክልሉ በአዲስ መልክ ከተደራጀ በኋላ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ዘርፎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት ተከናውነዋል፡፡

በዚህም የተመዘገቡ ስኬቶች እንዳሉ ገልጸው፣ የስኬቶችን ቀጣይነት ለማረጋገጥ ተሞክሮዎችን ማስፋት፣ ማነቆዎችን መፍታትና በቅንጅት መስራት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡

በቀጣይም ድህነትን በሚቀንሱ ተግባራት ላይ በማተኮር ገበያን ማረጋጋት፣ ለወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠርና የቤተሰብ ብልጽግናን ማረጋገጥ የክልሉ መንግስት ትኩረቶች መሆናቸውን አስረድተዋል።

ለዚህም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአቅርቦት እጥረት ችግርን በመፍታት የእያንዳንዱን ቤተሰብ ህይወት ለመቀየር የተቀረጸውን ፓኬጅ በመተግበር የህብረተሰቡን ገቢ ለማሳደግ ይሰራል ብለዋል፡፡

በክልሉ ለወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠር የተገኙ ውጤቶች አበረታች መሆናቸውን የገለጹት ርዕሰ መስተዳደድሩ፣ በቀጣይ ተጨማሪ የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ቀድመው ወደሥራ የገቡትን  የመደገፍ ሥራ ይሰራል ብለዋል፡፡

መልካም አስተዳደርን ለማስፈን የተጀመሩ ሥራዎች እያስገኙ ያሉትን ውጤት በማስቀጠል በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የህዝብን እርካታ ማረጋገጥ ሌላው ትኩረት መሆኑንም ጠቅሰዋል። 

በውይይት መድረኩ ከክልሉ መንግስት ዕቅድ ጋር የሚጣጣሙ ሀሳቦች መንጸባረቃቸውን ገልጸው፣ የክልሉን እድገት ለማፋጠን  ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት ይሰራል ብለዋል።

የክልሉን የአምስት ዓመታት ጉዞ ሰነድ ለውይይት ያቀረቡት የክልሉ ፕላንና ልማት ቢሮ ሃላፊ አራርሶ ገረመው (ዶ/ር) በበኩላቸው በመሰረተ ልማት ዘርፍ የተከናወኑ ሥራዎች ለህዝብ ጥያቄ ምላሽ የሰጡ ናቸው ብለዋል።


 

በዚህም ባለፉት አምስት ዓመታት ከ2 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ከ1 ሺህ 400 ኪሎ ሜትር በላይ የመንገድ ግንባታ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል።

የክልሉን የመጠጥ ውሃ ሽፋኑን ወደ 64 በመቶ ያሳደጉ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት መብቃታቸውንም  ተናግረዋል፡፡

በትምህርት ዘርፍም ቅድመ መደበኛ ላይ ትኩረት በማድረግ ባለሃብቱንና ህዝቡን በማስተባበር የአዳዲስ ትምህርት ቤቶች ግንባታ መከናወኑን ገልጸው፣ በዚህም ከፍተኛ ለውጥ መታየቱንም ጠቁመዋል፡፡

አራርሶ (ዶ/ር) እንዳሉት በግብርና፣ በእንስሳትና ዓሣ ሃብት ልማት ምርታማነትና ገቢን ለማሳደግ የተሰሩ ሥራዎችም በክልሉ ኢኮኖሚ ላይ ጉልህ ድርሻ አላቸው፡፡

የሲዳማ ክልል ከተደራጀ በኋላ በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎችና በሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ባለፉት አምስት ዓመታት የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ትናንት በተለያዩ ባለድርሻ አካላት ተጎብኝተዋል።

በዛሬው መድረክም በመስክ ምልከታ በታዩ ጉዳዮችና በቀረበው ሰነድ ላይ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት በጋራ መክረዋል።

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም