የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ስልጠና አካዳሚ ለአፍሪካ ሀገራት ተመራጭ የስልጠና ማዕከል እየሆነ ይገኛል - የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን በለስልጣን

አዲስ አበባ፤ሰኔ 24/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን የስልጠና አካዳሚ ለበርካታ የአፍሪካ ሀገራት ቀዳሚ ተመራጭ የስልጠና ማዕከል እየሆነ እንደሚገኝ የኤር ናቪጌሽን ሬጉሌሽን አገልግሎት ዳይሬክተር እና የአካዳሚው ተጠባባቂ ዳይሬክተር ልዑልሰገድ ጉልላት ገለጹ።

ዳይሬክተሩ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ አካዳሚው ለአቪዬሽን ኢንዱስትሪው ውጤታማነት ባለሙያዎችን በማፍራት ላይ ይገኛል ብለዋል።  

ለበርካታ ዓመታት በአየር ትራፊክ ቁጥጥር፣ በኮሙኒኬሽን እና ናቪጌሽን ሰርቪላንስ (CNC) ዘርፍ በአገሪቱ የተለያዩ ክልሎች ብቁ የአቪዬሽን ባለሙያዎችን በማሰማራት ላይ መሆኑንም ጠቅሰዋል።


 

በዚህ ዓመት ብቻ ከ86 በላይ ባለሙያዎችን በንድፈ ሃሳብና በተግባር የተደገፈ ስልጠና በመስጠት ወደ ሥራ ማስገባቱን አንስተዋል።

አካዳሚው የሚሰጠው ስልጠና ከሀገር አልፎ ለጎረቤት ሀገራትና ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ውጤታማ ስልጠና እየሰጠ ተፈላጊነቱን እያሳደገ ይገኛል ብለዋል።

በቅርቡ ከጅቡቲ፣ ከሶማሊያ እንዲሁም ከኮሞሮሶና ሌሎች ሀገራት የመጡ የአቪዬሽን ሰልጣኞችን ማሰልጠኑን ተናግረዋል።

በርካታ የአፍሪካ ሀገራት በኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን የስልጠና አካዳሚ ሙያተኞቻቸውን ለማሰልጠን ጥያቄ እያቀረቡ እና ተመራጭ እያደረጉት መሆኑን ተናግረዋል።  

አካዳሚው በአፍሪካ ትልቅ ስምና ተቀባይነት እንዳለው በማንሳት፥  ይበልጥ ቀጣናውን ለማስተሳሰር በርካታ ተግባራትን በትኩረት እያከናወነ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።


 

በአካዳሚው አሰልጣኝ እና ዋና የአየር ተቆጣጣሪ ቤተልሔም ሞላ በበኩላቸው፥ ስልጠናው የዓለም አቪዬሽን ኢንዱስትሪ በደረሰበት ደረጃ  ልክ እየተሰጠ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

በተግባር እና በንድፈ ሀሳብ የተደገፈው ስልጠና ሰልጣኞች ተግባራዊ የሆነ በቂ እውቀት የሚያገኙበት እና በአቪዬሽን ኢንዱስትሪው ውጤታማ የሚያደርጋቸው ነው ብለዋል። 

ባለፉት ሰባት ወራት በብቁ አሰልጣኞች በንድፈ ሀሳብና በተግባር የተደገፈ ስልጠና መውሰዱን የገለጸልን ደግሞ ከድሬዳዋ የመጣው ምንተስኖት አለማየሁ  ነው።


 

በአቪዬሽን ዘርፉ በተሰማራበት ሙያ ለማገልገል ካለው ተነሳሽነት በተጨማሪ፥ በስልጠናው ያገኘው እውቀት ትልቅ አቅም እንደፈጠረለትም ተናግሯል። 

 

 

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም