ኢትዮጵያ በአራተኛው የዘላቂ ልማት ፋይናንስ ኮንፈረንስ ላይ እየተሳተፈች ትገኛለች

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 23/2017(ኢዜአ)፦ በስፔን ሲቪያ እየተካሔደ ባለው አራተኛው አለም ዓቀፍ የዘላቂ ልማት ፋይናንስ ኮንፈረንስ ላይ በግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ(ዶ/ር) የተመራ የኢትዮጵያ ልኡክ እየተሳተፈ ይገኛል።

ኮንፈረንሱ እኤአ ከጁን 30 እስከ ጁላይ 3/2025 እንደሚካሔድም ታውቋል።

የልዑክ ቡድኑ በኮንፈረንሱ በሚያደርገው ተሳትፎ በተለያዩ መርሃ-ግብሮች ኢትዮጵያን በመወከል ተሳትፎ የሚያደርግ ይሆናል።

ከኮንፍረንሱ ጎን ለጎን Global Alliance Against Poverty and Hunger የትይዩ ስብሰባ ያዘጋጀ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ በብራዚል የG20 ሊቀ መንበርነት የተቋቋመው የዚሁ Alliance የሻምፕዮኖች የቦርድ አባል እንደመሆኗ በሌማት ትሩፋት ዙሪያ ያላት ልምድ እንደ ተምሳሌታዊ ፕሮጀክት በግብርና ሚኒስትሩ በኩል ይቀርባል።


 

ኢትዮጵያ በሌማት ትሩፋት ያስመዘገበችውን ውጤት በኮንፈረንሱ ላይ በተሞክሮነት ከማጋራት በተጨማሪ ሀገራችን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የምታደርጋቸውን ሌሎች ሰፋፊ ጥረቶች ሚኒስትሩ እንደ ልምድ የሚያቀርቡ ይሆናል።

አራተኛው አለም ዓቀፍ የዘላቂ ልማት ፋይናንስ ኮንፈረንስ የዘላቂ ልማት ግቦችን እ.አ.አ በ2030 ለማሳካት በዋነኛነት ማነቆ የሆነውን የልማት ፋይናንስ ተግዳሮት ለመፍታት የመፍትሄ አቅጣጫዎችን ያስቀምጣል ተብሎ እንደሚጠበቅ ሚኒስቴሩ ለኢዜአ የላከው መረጃ ያሳያል።

ሶስተኛው አለም አቀፍ የዘላቂ ልማት ፋይናንስ እ.አ.አ በ2015 በአዲስ አበባ መካሄዱ ይታወሳል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም