የፀሃይ ሃይል አማራጭን በመጠቀም የኤሌክትሪክ አገልግሎቱን ተደራሽ ለማድረግ እየተከናወነ ያለው ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል - ኢዜአ አማርኛ
የፀሃይ ሃይል አማራጭን በመጠቀም የኤሌክትሪክ አገልግሎቱን ተደራሽ ለማድረግ እየተከናወነ ያለው ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል

ጋምቤላ፤ ሰኔ 19/2017 (ኢዜአ) የፀሃይ ሃይል አማራጭን በመጠቀም የኤሌክትሪክ አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ እየተከናወነ ያለው ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) ገለፁ።
በጋምቤላ ክልል በኑዌር ዞን በዋንቱዋ ወረዳ መታር ከተማ የተገነባው በፀሀይ ብርሃን የሚሰራ የሀይል ማመንጫ ፕሮጀክት የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት ዛሬ ተመርቋል።
ሚኒስትር ዴኤታው ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) በፕሮጀክቱ የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ ተገኝተው እንዳሉት የህዝቡን ህይወት ለመቀየር እየተከናወኑ ካሉ ስራዎች መካከል አንዱ የሃይል አቅርቦትን ተደራሽ ማድረግ ነው ብለዋል።
በተለይም ያሉንን የተፈጥሮ ፀጋዎች ተጠቅመን በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች የኤሌክትሪክ ሃይል ተደራሽ ለማድረግ የሚከናወነው ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ዛሬ በጋምቤላ ክልል በመታር ከተማ ተገንብቶ ለአገልግሎት የበቃው የፀሐይ ሃይል ማመንጫ ፕሮጀክትም የዚሁ ስራ አንዱ አካል መሆኑን ገልፀዋል።
እንደ ሀገር የኤሌክትሪክ ሃይል አማራጮችን በማስፋት የህዝቡን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትኩረት መሰጠቱን አብራርተዋል።
የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር) በበኩላቸው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የመረቀው የፀሃይ ሃይል ለክልሉ የልማት ስራዎች ውጤታማነት የላቀ አበርክቶ አለው ብለዋል።
አገልግሎቱ በክልሉ የሚገኙ ከተሞችንና የገጠር ቀበሌዎችን የሃይል አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ የጀመረው ጥረትም የሚበረታታ መሆኑን ተናግረዋል።
በመታር ከተማ ተገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው የፀሐይ ሀይል ማመንጫ ፕሮጀክት የአካባቢውን ህዝብ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያፋጥን መሆኑን ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የኮሙኒኬሽን ስራ አስፈፃሚ አቶ አንዋር አብራር በበኩላቸው እንደ ሀገር ህዝቡን ፍትሃዊ የኤሌክትሪክ ሀይል አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ ብለዋል።
በተለይም ከዋና የኤሌክትሪክ መስመር በርቀት ላይ የሚገኙ የገጠር ከተሞችንና መንደሮችን የፀሐይ ሃይል አማራጭ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚ ማድረግ ትኩረት እንደተሰጠውም ገልፀዋል።
ከመታር ከተማ ነዋሪዎች መካከል አቶ ተስሉዋች ኮክ እና ወይወሮ ሳራ ኛቺን በሰጡት አስተያየት በአካባቢያቸው የፀሐይ ሀይል ማመንጫ ተገንብቶ ለአገልግሎት መብቃቱ ባለፉት ዓመታት ሲነሱ ለነበሩ የህዝብ ጥያቄዎች ምላሽን የሰጠ ነው ብለዋል።
ከአፍሪካ ልማት ባንክ በተገኘው 69 ሚሊዮን ብር ድጋፍ እና መንግስት በመደበው ቀሪ 27 ሚሊዮን ብር በድምሩ 96 ሚሊዮን ብር መታር ከተማ ላይ የተገነባው የፀሃይ ኃይል አማራጭ ፕሮጀክት 250 ኪሎ ዋት የማመንጨት አቅም ያለው ሲሆን ከሶስት ሺህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ያደርጋል።
እንደ ሀገር በተለያዩ ክልሎች 18 የፀሐይ ሀይል ማመንጫ ፕሮጀክቶችን በመገንባት የህዝቡን የሀይል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑንም ከአገልግሎት መስሪያ ቤቱ የተገኘው መረጃ ያመላክታል ።