የጅግጅጋ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ውበትና ድምቀት እያጎናጸፋት ነው - ኢዜአ አማርኛ
የጅግጅጋ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ውበትና ድምቀት እያጎናጸፋት ነው

ጅግጅጋ ፤ሰኔ 12/2017 (ኢዜአ) የጅግጅጋ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ውበትና ድምቀት እያጎናጸፋት መሆኑን ነዋሪዎች ገለጹ።
የጅግጅጋ ከተማ ኮሪደር የመጀመሪያ ምዕራፍ ልማት 10 ኪሎ ሜትር መንገዶች በ6 ሳይቶች ላይ እየተከናወነ ነው ።
የኮሪደር ልማቱን አስመልክቶ ኢዜአ ያነጋገራቸው የጅግጅጋ ከተማ ነዋሪዎች የኮሪደር ልማቱ የከተማውን ገጽታ እንደሚጨምር ተናግረዋል።
ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል መምህር ሙሳ ሃጂ፤ ኮሪደር ልማቱ ከተማዋን ለስራና ለኑሮ ምቹ ከማድረጉ ባለፈ ለአካል ጉዳተኞች ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ለመንቀሳቀስ አስቸጋሪ የነበረን ሁኔታ መቀየሩን አስረድተዋል።
ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ ፋራህ ዑመር በበኩላቸው ኮሪደሩ ጠባብና ለእንቅስቃሴ አስቸጋሪ የነበረን የከተማዋን መንገድ በማስፋት ከተሽከርካሪዎች አደጋ ራስን ለመጠበቅ ምቹ አጋጣሚ የፈጠረ ነው ብለዋል።
የኮሪደር ልማቱ የከተማዋን እንቅስቃሴ እንዲሳለጥ፣ ለአካባቢያቸው እድገትም ትልቅ እድል መሆኑንና ከተማዋን ውበትና ድምቀት እያጎናጸፋት መሆኑን ገልጸዋል።
የኮሪደር ልማቱ የእግረኞች፣ የተሽከርካሪዎች እና የሳይክል መንገዶች ማካተቱ የከተማዋን የትራንስፖርት እንቅስቃሴ እንደሚያሳልጠው የገለጹት ደግሞ ሌላኛው የከተማ ነዋሪ አቶ አብራሃም ተፈሪ ናቸው ።
ይህንን ተሞክሮም ወደ ሌሎች የክልሉ ከተሞች ማስፋት እንደሚገባም አመልክተዋል።
የጅግጅጋ ከተማ ከንቲባ ኢንጅነር ሻፊ መአልን፤ የኮሪደር ልማቱ የከተማዋ ነዋሪዎች የመልካም አስተዳደር ጥያቄ የነበረውን የመሰረተ ልማት ተደራሽነት እየፈታ መሆኑን አንስተዋል።
የኮሪደር ልማቱ የከተማዋን የ30 አመታት የእድገት ዲዛይን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ጠቁመው ይህን ለማሳካት ከነዋሪዎች ጋር በመወያየት ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል።
በኮሪደር ልማቱ የተካተቱት 10 ኪሎ ሜትር የሚሸፍኑ ስድስት የአስፋልት መንገዶች ግንባታም 85 በመቶ መድረሱን ተናግረው የመንገዶቹ ግንባታ ቀደም ሲል ይደርስ የነበረን የጎርፍ አደጋን እንደሚያስቀርም ጠቁመዋል።
በኮሪደር ልማቱ 5 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ ፓርክ፣ የህጻናት መጫወቻ ቦታዎች፣ የመዝናኛ ሥፍራዎች እና ካፍቴሪያዎች መካተታቸውን አክለዋል።
የኮሪደር ልማቱ እስካሁን በተጠናቀቀባቸው አካባቢዎች የተሽከርካሪዎችና የእግረኞች መንገድ እንዲሰፋ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰው ለረጅም ጊዜ የሚያገለግሉ መሠረተ ልማቶችን በማስተሳሰር በመሬት ስር እንዲሄዱ መደረጉንም ጠቁመዋል።
ከዚህ ባለፈም ልማቱ በከተማው ለ12 ሺህ 500 ዜጎች የሥራ እድል እንደፈጠረላቸው ገልጸዋል።