ለከተማዋ ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርጉ ባለሙያዎች እያፈራን ነው- ከንቲባ አዳነች አቤቤ

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ለሰው ሃይል ልማት ቅድሚያ ሰጥተን በመስራታችን ለአዲስ አበባ  ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክቱ ባለሙያዎች እያፈራን እንገኛለን ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ተናገሩ፡፡

ከንቲባ አዳነች አቤቤ “ብሩህ  አዕምሮዎች  በክህሎት የበቁ ዜጎች” በሚል መሪ ቃል የሚከበረውን 15ኛውን ከተማ አቀፍ የቴክኒክና ሙያ አውደ ርዕይ መርቀው ከፍተዋል።


 

አውደ ርዕዩ ከዛሬ ጀምሮ ለአምስት ቀን ክፍት ሆኖ አንደሚቆይ ተገልጿል፡፡

ከንቲባ አዳነች በዚሁ ወቅት እንደገለጹት ኢትዮጵያ በርካታ የልማት ተግባራትን በማከናወን የብልጽግና መሰረት እየጣለች ትገኛለች፡፡

ኢትዮጵያ የምትበለጽገው የራሳችንን የሰው ሀይልና  የተፈጥሮ ሀብት አቀናጅተን በማልማት ነው በሚል ጽኑ አቋም በሰራናቸው ስራዎች የብልጽግና መሰረት እየተጣለ ይገኛል ብለዋል።

በዚህም አዲስ አበባን የብልጽግና ማሳያ ለማድረግ የከተማ አስተዳደሩ ቀን ከሌት በትኩረት እየሰራ ይገኛል ነው ያሉት፡፡

እየተከናወኑ ባሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ተግባራት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ከፍተኛ ውጤቶች እየተመዘገቡ መሆኑንም አንስተዋል፡፡

በሰው ሃይል ልማት ላይ በተሰራው ስራ በከተማዋ ልማት  አሻራቸውን  ያሳረፉ ባለሙያዎችን ማፍራት መቻሉን አንስተዋል፡፡


 

የቴክኒክና ሙያ ዕውቀትን የቀሰሙ ባለሙያዎች ለከተማዋ ልማት ትልቅ እገዛ የሚያደርጉ የተለያዩ ችግር ፈቺ ማሽኖችን እያመረቱ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡

የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ለኮሪደር ልማቱ ብቁ የሰው ሃይል በማቅረብና የተለያዩ ማሽኖችን በማምረት ያበረከቱትን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ለአብነት አንስተዋል፡፡

የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ጥራት ያለው ተኪ ምርት በማምረት ከውጭ የሚገባ ምርትን በማስቀረት ረገድ የራሳቸውን ሚና እየተጫወቱ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡

ከንቲባዋ በዘርፉ የሚነሱ ጥያቄዎችን በመፍታት እና የሚደረገውን ድጋፍ በማጠናከር የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ሚና የበለጠ እንዲጠናከር ይደርጋል ብለዋል።

በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ስራና ክህሎት ቢሮ ሀላፊ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው ከተማ አስተዳደሩ ባለፉት ሰባት አመታት ከፍተኛ ገንዘብ በመመደብ ተቋማቱን በወርክሾፕ፣ በመሰረተ ልማት፣ በማሽነሪ እና በሰው ሃይል የማጠናከር ስራ ማከናወኑን አስታውቀዋል።

በተሰራው ውጤታማ ስራ ኮሌጆቹ ፍላጎት ያላቸው ወጣቶች ሙያ የሚቀስሙባቸው ተቋማት ለመሆን መብቃታቸውን ጠቅሰዋል፡፡

አውደ ርዕዩ ህብረተሰቡ በዘርፉ የተፈጠረውን አቅም እንዲገነዘብ ለማድረግ የተዘጋጀ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡

በአውደ ርዕዩ ከ150 በላይ የፈጠራ ውጤቶች ለእይታ የሚቀርቡ ሲሆን የፓናል ውይይቶችና ሌሎች መርኃ ግብሮች እንደሚካሄዱ ተመላክቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም