ቋሚ ኤግዚቢሽኑ የነገዋን ኢትዮጵያ የምንሰራበት ትልቅ ሀብት የያዘ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
ቋሚ ኤግዚቢሽኑ የነገዋን ኢትዮጵያ የምንሰራበት ትልቅ ሀብት የያዘ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ የሳይንስ ሙዚየም ቋሚ ኤግዚቢሽን የነገዋን ኢትዮጵያ የምንሰራበት እና የምንገነባበት ትልቅ ሀብት የያዘ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ።
ኤግዚቢሽኑ ልጆች የነገ ማንነታቸው እንዲሰራ እና የነገ መሻታቸው እውን እንዲሆን የሚያደርግ ነውም ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት የሳይንስ ሙዚየም ቋሚ ኤግዚቢሽን ክፍል ዛሬ በይፋ ተከፍቷል።
ኤግዚቢሽኑ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ፣ የአየር ንብረት ለውጥ እና የኢትዮጵያ ምላሽ፣ ግብርና፣ የውኃ ኃይል እና ኢነርጂ፣ ኤሮኖቲክስ እና አቪየሽን ላይ ያተኮሩ አምስት የዐውደ ርዕይ ምድቦችን የያዘ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሳይንስ ሙዚየም ሕንጻ ከሁለት ዓመት ገደማ በፊት ተገንብቶ በጊዜያዊ ኤግዚቢሽን መመረቁን አስታውሰዋል።
ቋሚ ኤግዚቢሽኑ ከፍተኛ ሀብት መጠየቁን ጠቁመው በጣም ጠቃሚ ነገር የያዘ መሆኑንና ነገን የምንሰራበት ሙዚየም እዚህ ነው ያለው ሲሉ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያውያን ነገን መስራት ነገን መለወጥ ከፈለጉ ልጆቻቸውን ወደ ኤግዚቢሽኑ ስፍራ ሊያመጧቸው እንደሚገባም አመልክተዋል።
ልጆች በሙዚየሙ ያሉ ነገሮችን በተግባር በማየት የነገ ማንነታቸውን መስራት እና የነገ መሻታቸውን እውን ማድረግ ይችላሉ ሲሉም ገልጸዋል።
ኤግዝቢሽኑ ለልጆች ታላቅ በረከት ይዞ መጥቷል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ልጆች ቴክኖሎጂን በሚገባ እንዲጠቀስሙ እና አልፎም ፈጣሪ እንዲሆኑ በር የሚከፍት ነው ብለዋል።
ወላጆች ቋሚ ኤግዚቢሽኑ ለልጆች ትልቅ ዕድል መሆኑን ተገንዝበው ወደ ስፍራው ይዘዋቸው እንዲመጡ እና መልካም ዘርን እንዲዘሩባቸው አስገንዝበዋል።
ይህንን እያየ ያደገ ልጅ ጥበብ እና እውቀትን በማዳበር ነገ ሀገሩን የሚጠብቅ፣ ሀገር የሚያበለጽግ፣ ሀገር የሚያለማ እና ሀገር የሚያጸና ይሆናል ሲሉም ተናግረዋል።
በተጨማሪም መምህራን፣ ተመራማሪዎችና ነገን መስራት የሚፈልጉ ሰዎች በሙሉ ኤግዚቢሽኑን እንዲጎበኙ ጥሪ አስተላልፈዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለቋሚ ኤግዚቢሽኑ ግንባታ ድጋፍ ላደረጉ ሀገራት እና ዓለም አቀፍ ተቋማት ምስጋና አቅርበዋል።