ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት የሳይንስ ሙዚየም ቋሚ ኤግዚቢሽን ክፍል በይፋ ተከፈተ

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት የሳይንስ ሙዚየም ቋሚ ኤግዚቢሽን ክፍል በይፋ ተከፍቷል።

ይኽ ድንቅ ክንውን በአርቴፊሻል ኢንተሊጀንስ፣ የአየር ንብረት ለውጥ እና የኢትዮጵያ ምላሽ፣ ግብርና፣ የውኃ ኃይል እና ኢነርጂ፣ ኤሮኖቲክስ እና አቪየሽን ላይ ያተኮሩ አምስት የዐውደ ርዕይ ምድቦችን የያዘ ነው።


 

ይኽም ሀገራችን ሳይንስ እና ቴክኖሎጂን ለመጠቀም ያላትን ጽኑ ፍላጎት የሚያሳይ ነው ሲል የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል።

በተጨማሪም በሀገራችን የመጀመሪያ የሆነው የህዋ ቅርጽ ሉላዊ የትእይንት አዳራሽም ይፋ ሆኗል።

በ1000 ሜትር ስኩዌር ሜትር እና 36 ሜትር ዲያሜትር ይዞ ያረፈው አዳራሽ ዘመኑን በዋጀ የ4k ዲጂታል ምስል ማሳያ ቴክኖሎጂ የተገጠመለት መሆኑንም ገልጿል።


 

ምስለ-ህዋው ከፍተኛ ጥራት ያለው እጅግ አስደማሚ ምስሎችን በማቅረብ የህዋውን አለም እጅግ አቅርቦ ያሳያል።

እውቀት ለማሰስ፣ ለመማር እና ለመነሳሳት ምቹ የሆነው የሳይንስ ሙዚየም ለጎብኚዎች ክፍት መሆኑንም አስታውቋል።

ህዝቡም መጥቶ የኢትዮጵያን የሳይንስ እና ቴክኖሎጂ መፃዒ ተስፋ እንዲመለከቱ ጽህፈት ቤቱ ጋብዟል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም