የህግ ታራሚዎች ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኙ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ይበልጥ ማሳደግ ይገባል

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ የህግ ታራሚዎች ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኙ ለማድረግ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ይበልጥ ማሳደግ እንደሚገባ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ቴዎድሮስ ምህረት ተናገሩ። 

የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ከፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጋር በመተባበር በኮሚሽኑ ከፍተኛ ጥበቃ ማረሚያ ማዕከል ለህግ ታራሚዎች አገልግሎት የሚውል የፕላዝማ ችሎት አገልግሎትና የኢ-ፋይሊንግ ሥርዓትን አበልፅጎ ወደ ስራ አስገብቷል።


 

የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት  ቴዎድሮስ ምህረት በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ማረሚያ ቤቶች የፍርድ ቤቶችን ውሳኔ የሚያስፈጽሙ በመሆናቸው ህገ-መንግስቱን፣ የኢትዮጵያንና የዓለም አቀፍ ህጎችን ባከበረ መልኩ ታራሚዎችን መያዝ ይገባቸዋል፡፡   

በዚህም የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ጋር በመተባበር የፕላዝማ ችሎት እና ኢ-ፋይሊንግ ሲስተም አበልፅጎ ወደ ስራ አስገብቷል ነው ያሉት። 

የቀጠሮ ምልልስ፣ እንግልት እና ጊዜን በአግባቡ ለመጠቀም ይህን ፕሮጀክት ወደ ስራ ማስገባት አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱን አንስተዋል።

ተቋማትን በቴክኖሎጂ በማዘመን የታራሚዎችን የፍትህ ጥያቄ በፍጥነት መመለስ እንደሚያስችል ገልጸው፤ የህግ ታራሚዎች ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኙ ለማድረግ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ይበልጥ ማሳደግ ይገባል ብለዋል።


 

የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጄኔራል የኑስ ሙሉ በበኩላቸው መንግስት ባስቀመጠው የሪፎርም አቅጣጫ መሠረት ማረሚያ ቤቶች ዜጎች ታርመውና ታንፀው አምራችና ህግ አክባሪ ሆነው ወደ ሠላማዊ ህይወት እንዲመለሱ አበረታች ተግባር መከናወኑን ተናግረዋል።

ለአገልግሎት ክፍት የተደረገው የፕላዝማ ችሎት አገልግሎት እና ኢ-ፋይሊንግ ሲስተም አንዱ ማሳያ መሆኑን በመጠቆም።

የሪፎርም ዕቅዱ ካስቀመጣቸው የትኩረት አቅጣጫዎች መካከል የህግ ታራሚዎችን የሰብዓዊ መብት አያያዝ ማሻሻል ነው ብለዋል።

የተጀመሩ የለውጥ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ኮሚሽነር ጄኔራሉ አረጋግጠዋል።

 

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም