የሳይበር ጥቃቶችን ለመቋቋም የሳይበር ደህንነት ላይ የሚሰሩ ምርምሮችን መደገፍ ያስፈልጋል - ሚኒስቴሩ

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ በየጊዜው የሚቀያየረውን የሳይበር ጥቃት ለመቋቋም የሳይበር ደህንነት ላይ የሚሰሩ ምርምሮችን መደገፍ እንደሚያስፈልግ የኢኖቬሸንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ገለጸ።

የኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ማህበር በሳይበር ደህንነት ላይ ትኩረት ያደረገ “ዓለም አቀፍ የሳይበር ደህንነት እና ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን በኢትዮጵያ" በሚል ሀሳብ ጉባዔ እያካሄደ ይገኛል።


 

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ፎዚያ አሚን(ዶ/ር) በጉባዔው መክፈቻ ላይ እንደተናገሩት፤ የሳይበር ደህንነትን ለማስጠበቅ የፈጠራ ስራዎች ወሳኝ ናቸው።

ይህንንም ውጤታማ ለማድረግ የሳይበር ደህንነት ላይ የሚከናወኑ ምርምሮችን መደገፍ አስፈላጊ ነው ብለዋል።

የሳይበር ደህንነት መሪ በሚሆነው ትውልድ ላይ መስራት እንደሚገባ ገልጸው፤ የሳይበር ደህንነት ላይ የሚሰሩ ምርምሮችን በማጠናከርና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተደራሽ በማድረግ በዘርፉ አዎንታዊ ሚና መጫወት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።

ከምሁራን፣ ከሲቪክ ማህበራትና ዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር በትብብር መስራት እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል።

የሳይበር ደህንነት የማስጠበቅ ስራን ስኬታማ ለማድረግ ትብብር ወሳኝ መሆኑን አመላክተው፤ በዘርፉ ያለውን እውቀት፣ መልካም ተሞክሮና ሀብት በመጠቀም በጋራ መስራት እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል።

የሳይበር ደህንነት ተግዳሮቶችን ለማስወገድና የጋራ መፍትሄዎችን ለመፍጠር ከአጋር አካላት ጋር የሚሰሩ ስራዎችን እንደሚጠናከሩም ተናግረዋል።

ጉባዔው የዲጂታል ዘርፉን ቀጣይ ምዕራፍ የሚያመላክት እና የዲጂታል ሽግግሩን ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ ግብዓት ለመሰብሰብ ያግዛል ነው ያሉት።


 

የዓለም አቀፍ የቴሌኮሙኒኬሽን ሕብረት የአፍሪካ ቀጣናዊ ዳይሬክተር ኢማኑኤል ማናሳህ እንዳሉት የዲጂታል ሽግግር ስራዎችን ለማጠናከር ትስስር መፍጠር፣ የዲጂታል ክህሎትና የፈጠራ ችሎታን ማዳበር ያስፈልጋል።

የሳይበር ደህንነትን ማስጠበቅ፣ መዋዕለ ነዋይን ማፍሰስ፣ ህግና ፖሊሲዎችን ማሻሻል እንዲሁም ምቹ ከባቢ መፍጠር ወሳኝ መሆኑን አክለዋል።

አፍሪካውያን በትብብር በመስራት ደህንነቱ የተጠበቀ፣ ተመጣጣኝና ቀልጣፋ የዲጂታል አገልግሎት እንዲጠናከር ማድረግ አለባቸው ብለዋል።


 

የኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ማህበር ፕሬዝዳንት ብርሃኑ በየነ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የሳይበር ደህንነት ስጋቶች ውስብስብና በየጊዜው ተለዋዋጭ በመሆናቸው አፍሪካውያን በጋራ መስራት ይኖርባቸዋል ብለዋል።

ይህም ዲጂታል እሴቶችን እና መሰረተ ልማቶችን መጠበቅ እንደሚያስችል ተናግረዋል።

ኮንፍረንሱ በሀገር እና በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚገኙ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ አካላት፣ ተመራማሪዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት የሀሳብና የልምድ ልውውጥ ለማድረግና በጋራ እንዲሰሩ እድል ይፈጥራል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም