ቀጥታ፡

ኢትዮጵያ ወደ ቻይና የምትልካቸውን ምርቶች በአይነትና በመጠን ለማሳደግ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ ነው-አምባሳደር ተፈራ ደርበው

አዲስ አበባ፤ሰኔ 5/2017 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ወደ ቻይና የምትልካቸውን ምርቶች በአይነትም በመጠን ለማሳደግ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን በቻይና የኢትዮጵያ አምባሳደር ተፈራ ደርበው ገለጹ።

አራተኛው የቻይና አፍሪካ የኢኮኖሚና ንግድ ኤክስፖ በቻይና ቻንግሻ ከተማ ዛሬ ተከፍቷል።

ከኤክስፖው ጎን ለጎንም የኢትዮጵያን የአኩሪ አተር ተረፈ ምርት በቻይና ለማቅረብ የሚያስችል ስምምነት መፈረሙን የኢዜአ ሪፖርተር ከስፍራው ዘግቧል።

ስምምነቱን በቻይና የኢትዮጵያ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ተፈራ ደርበውና የቻይና የጉምሩክ አጠቃላይ አስተዳደር ምክትል ሚኒስትር ዋንግ ልንግጁን ተፈራርመውታል።

አምባሳደሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ስምምነቱ ለኢትዮጵያ አዲስ የገበያ እድል ከማስገኘቱ በተጨማሪ ወደ ቻይና የሚላኩ ምርቶችን መጠን ከፍ የሚያደርግ ነው።

ስምምነቱ ባለፉት ስድስት ወራት በኢትዮጵያ የግብርና ባለስልጣንና በቻይና ጉምሩክ ባለስልጣን በጋራ ሲዘጋጅ መቆየቱን አንስተዋል።

ስምምነቱ ከሀገሪቱ ጋር ያለውን የንግድ ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚረዳ ገልጸው፤ኢትዮጵያ ወደ ቻይና የምትልካቸውን ምርቶች በአይነትም በመጠንም ለማሳደግ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ ነው ብለዋል።

በተመሳሳይም አምባሳደር ተፈራ 'ከቻንግሻ ሳተርንበርድ ኮፊ ኤልቲዲ' (Changsha Saturnbird Coffee Co., LTD.) መስራች እና ሊቀመንበር ሚስተር ው ጁን ጋር የኢትዮጵያ ቡናን እሴት ጨምሮ ለቻይና ገበያ ለማቅረብ እንዲችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል።

ኩባንያው የኢትዮጵያ ቡናን በብዛት በመግዛት ለሌሎች የቻይና ቡና ኩባንያዎች ለማከፋፈል፣ ቆልቶ ለማዘጋጀት፣ለመፍጨት እና የቡና ምርቶች ለማዘጋጀት እንደግብዓት የሚጠቀም መሆኑ ተገልጿል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም