በበጀት አመቱ በአገር-አቀፍ ደረጃ ተፈጻሚ የሚሆኑ 18 አስገዳጅ ደረጃዎች ጸድቀው ወደ ስራ ገብተዋል

አዲስ አበባ፤ሰኔ 4/2017(ኢዜአ)፦ በ2017 በጀት አመት በአገር-አቀፍ ደረጃ ተፈጻሚ የሚሆኑ 18 አስገዳጅ ደረጃዎች ጸድቀው ወደ ስራ መግባታቸውን የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲቱዩት ዋና ዳይሬክተር መሰረት በቀለ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡

ኢዜአ ያነጋገራቸው የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር መሰረት በቀለ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩቱት ስራ ከጀመረ ከ50 አመት በላይ ማስቆጠሩን ተናግረዋል፡፡

በእነዚህ አመታት አለም አቀፍ አሰራርን ተከትሎ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ ለተለያዩ ምርቶችና አገልግሎቶች ብሔራዊ የጥራት ደረጃዎችን ሲያዘጋጅ መቆየቱን ተናግረዋል፡፡

እስካሁን ድረስም ከ12 ሺህ በላይ ብሔራዊ የጥራት ደረጃዎችን አዘጋጅቶ ስራ ላይ እንዲውሉ ማድረግ መቻሉን ነው የተናገሩት፡፡

ከነዚህ ደረጃዎች ውስጥ 414 የሚሆኑት የምርትና የአገልግሎት አይነቶች አስገዳጅ ደረጃዎች መሆናቸውን አመላክተዋል፡፡

በሰው ህይወት፣በእንስሳት፣ በእጽዋት፣በአካባቢ እና በብሔራዊ ደህንነት ላይ አደጋ የሚያስከትሉ ምርትና አገልግሎቶች አስገዳጅ ደረጃ እንደሚወጣላቸው ጠቁመዋል፡፡

በ2017 በጀት አመት በአገር አቀፍ ደረጃ ተፈጻሚ የሚሆኑ 18 አስገዳጅ ደረጃዎች ጸድቀው ወደ ስራ መግባታቸውን ተናግረዋል፡፡

ኢንስቲቱዩቱ በምርት ጥራት መጓደል የሚከሰቱ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ለመከላከል በወጪ፣በገቢ እና በአገር ውስጥ ጥቅም ላይ በሚውሉ ምርቶች ላይ የሚለጠፉ የጥራት ደረጃ ምልክቶችን አዘጋጅቶ ወደ ስራ ማስገባቱን ተናግረዋል፡፡

ለተግባራዊነቱም ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

የጥራት ምልክቶቹ ተመሳስለው የሚመረቱ ህገ-ወጥ ምርቶችን ከትክክለኛው ምርት ለመለየት የሚያስችሉ ናቸው ብለዋል፡፡

አምራቾች በሚያመርቷቸው ምርቶች ላይ የጥራት ደረጃ ምልክቶችን መጠቀም እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም