የኢትዮጵያ ልዩ መለያ የሆኑ የግብርናና የዕደ-ጥበብ ፈጠራ ውጤቶች የባለቤትነት መብት መረጋገጥ ለዘርፉ ዕድገት ጉልህ ሚና ይኖረዋል

አዲስ አበባ፤ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ልዩ መለያ የሆኑ የግብርናና የዕደ ጥበብ ፈጠራ ውጤቶች የባለቤትነት መብት መረጋገጥ ለዘርፉ ዕድገት ጉልህ ሚና እንደሚኖረው አምራቾች ገለጹ።

ኢትዮጵያ ቡናን ጨምሮ ልዩ ጣዕምና ባህሪ ያላቸው የግብርና ምርቶችን በስፋት የምታበቅል መሆኗ ይታወቃል።

በተለያዩ አካባቢዎች የሚመረቱ የእጅ ጥበብና የግብርና ምርቶችም በልዩ ባህሪያቸው በቀላሉ ይለያሉ።

እነዚህ ምርቶች ተገቢውን ዕውቅና አግኝተው አምራቹን ተጠቃሚ እንዲያደርጉና አገሪቷን በሚገባው ልክ እንዲያስተዋውቁ ብዙ ስራ መስራትን ይጠይቃል።

የባህል አልባሳት አምራች ወንድወሰን ይርጋለም፥ የባህል አልባሳት የኢትዮጵያ ልዩ መለያ በመሆናቸው የእጅ ጥበቡን ጠብቆ ለትውልድ ማስተላለፍ ይገባል ብሏል።

በባህል አልባሳት ዲዛይን ላይ የሚደረጉ ፈጠራዎች ተገቢውን የባለቤትነት ዕውቅና ቢያገኙ ለፈጠራው ባለቤትም ሆነ ለሌሎች አምራቾች መነሳሳትን እንደሚፈጥር ተናግሯል።


 

በሸክላ ስራ ላይ የተሰማሩት መዓዛ አሰግድና በእጅ ጥበብ ሥራ የተሰማሩት ትዝታ ሞረዳ በቡላቸው፣የእጅ ጥበብ ውጤቶቹ የተለያየ ፈጠራ ታክሎባቸው የኢትዮጵያን ባህል በሚያስተዋውቅ መልኩ እንደሚሰሩ ገልጸዋል።

የዕደ ጥበብ ውጤቶች እንደአካባቢው የተፈጥሮ ሃብትና የህብረተሰቡ የአኗኗር ዘይቤ የሚለያዩ ቢሆንም የኢትዮጵያን ብዝሃነትና ቱባ ባህል በማሳየት ረገድ ፋይዳቸው የጎላ መሆኑንም ነው ያነሱት።

ከትውልድ ትውልድ ሲተላለፍ የቆየውን የዕደ ጥበብ ውጤት ጠብቆ ለማቆየት ለባለሙያዎቹ ተገቢው የፈጠራ ባለቤትነት መብት ሊሰጥ እንደሚገባ ተናግረዋል።


 

የጋሞ ገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበር አትክልትና ፍራፍሬ አምራች ሲሳይ ቦጋለ በበኩላቸው፣ በአካባቢያቸው የሚበቅሉት የተለየ ጣዕም ያላቸው የፍራፍሬ ምርቶች በተጠቃሚዎች ዘንድ ተወዳጅ መሆናቸውን ያነሳሉ።

ማንጎና ሙዝን ጨምሮ እነዚህ ልዩ ጣዕምና ዕውቅና ያላቸው ምርቶች ጥራትና ተወዳጅነታቸውን ጠብቀው እንዲቆዩ እውቅና መሰጠቱ አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡

በኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ሰርተፊኬሽን ማዕከል የቡና ከፍተኛ ጣዕም መርማሪ ግሩም መኮንን፣ኢትዮጵያ የተለያየ ጣዕም ያላቸው የቡና ዝርያዎች የሚመረቱባት አገር መሆኗን ያነሳሉ።


 

እነዚህ የቡና ዝርያዎች ከሚመጡበት አካባቢ ስያሜ እንደሚያገኙና የታጠቡና ያልታጠቡ ተብለው እንደሚለዩ አመልክተዋል።

ቡናዎች እንደየመጡበት አካባቢ የጥራት ደረጃቸውን ጠብቀው ተወዳዳሪ ዋጋ እንዲያገኙ ለአምራቹ ተገቢው ዕውቅና ሊሰጥ ይገባል ብለዋል።

በአለም አቀፍም ሆነ በአገር ደረጃ ልዩ ጣዕም ያላቸውን ቡናዎች ጥራትና ተወዳዳሪነት ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ወልዱ ይመስል በበኩላቸው፥ የኢትዮጵያ ልዩ ባህሪ ያላቸው ምርቶችና የዕደ-ጥበብ ውጤቶችን የፈጠራ ባለቤትነትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥራዎች መጀመራቸውን ገልጸዋል።


 

በተለይም ምርቶቹ በመልክዓ ምድራዊ አቀማመጥና በልዩ ባህሪያቸው ተለይተው ለገበያ እንዲቀርቡ የሚያስችሉ ሰነዶች እየተዘጋጁ መሆኑንም ነው የተናገሩት።

ምርቶቹ በተመረቱበት አካባቢ ባሉ የህብረት ስራ ማህበራት የጥራት ደረጃቸው ተመዝግቦ የማረጋገጫ ሰርተፊኬት እንዲሰጣቸው ይደረጋል ብለዋል።

ይህም ምርቶች እንዳይደበላለቁ እንዲሁም ለፈጠራ ባለቤቶች ዕውቅና ለመስጠት ያስችላል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም