የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ የኮደርስ ስልጠናን እንዲወስዱ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስገኙ ነው - የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦ የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ስልጠናን እንዲወስዱ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስገኙ መሆኑን የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ገለፀ።

የ“አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ’’ መርኃ ግብር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ይፋ የተደረገ ሲሆን በኢትዮጵያ እና በተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መንግሥታት ትብብር እየተተገበረ ይገኛል።

ፕሮጀክቱ "ትውልድ ይማር፣ ትውልድ ይሰልጥን፣ ከዓለም ጋር ይፎካከር" በሚል እሳቤ ወጣቶች የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን በማዳበር በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እና ብቁ ማድረግ የሚያስችል ነው።

መርኃ ግብሩ በቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት የሚያስጨብጥ ነው።


 

የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የኤሌክትሮኒክስ ትምህርት ክፍል ዳይሬክተር መኮንን አበበ(ዶ/ር) የአምስት ሚሊየን ኮደርስ መርኃ ግብር ዜጎችን ከአለም ቴክኖሎጂ ጋር የሚያስተሳስር ነው ብለዋል።

የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች እና ማህበረሰብ ስልጠናውን እንዲከታተሉ ለማድረግ ሲሰራ መቆየቱን አስታውሰው በዚህም ስልጠናውን የተከታተሉ ተማሪዎችና ሰራተኞች ቁጥር ከ2ሺህ 800 መሻገሩን ተናግረዋል።

እስካሁን ባለው ሂደት 68 መምህራንና ከ730 በላይ የአስተዳደር ሰራተኞች ስልጠናውን ማጠናቀቃቸውንም ጠቅሰዋል።

የኮደርስ ስልጠና የተማሪዎችን የዲጂታል ክህሎት የሚያሳድግ መሆኑን ተከትሎ ስልጠናውን በስፋት እንዲወስዱ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

በዚህም 1ሺህ 80 የመጀመሪያ አመት እንዲሁም ከሁለተኛ አመት በላይ ያሉ 983 ተማሪዎች ስልጠናውን ማጠናቀቃቸውን አብራርተዋል።

የኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ክህሎትንና ተወዳዳሪነትን የሚያሳድግ በመሆኑ ሁሉም ስልጠናውን ቢከታተል ተጠቃሚ እንደሚሆንም አስገንዝበዋል።


 

በዩኒቨርሲቲው የኤሌክትሪካልና ኮምፒውተር ምህንድስና ተማሪ ሰለሞን ታረቀኝ የኮደርስ ስልጠና ለትምህርቱ እገዛ እንደሚያደርግለት ገልጿል።


 

ሌላው የኤሌክትሪካልና ኮምፒውተር ምህንድስና ተማሪ ቅዱስ ማሞ የኮደርስ ስልጠናን መውሰዱ በተለይ የጥናት ስራን ለማካሄድ እንደሚጠቅመው ተናግሯል።

ስልጠናው የዲጂታል ክህሎትን የሚያሳድግ በመሆኑ ሁሉም ተማሪ የተመቻቸውን ዕድል በመጠቀም ሊከታተለው እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም