በከተማዋ ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎት ለመስጠት 278 አገልግሎቶች በበይነ መረብ እንዲሰጡ ተደርጓል - ቢሮው

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎት ለመስጠት 278 አገልግሎቶች በበይነ መረብ እንዲሰጡ ማድረግ መቻሉን የአዲስ አበባ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ አስታወቀ።

ቢሮው የአዲስ አበባ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ እና የመዲናዋ ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን አገልግሎትን ማዘመን የሚያስችለውን የስማርት ኦፊስ ስራ ሰኔ 1 ቀን 2017 ዓ.ም ወደ ስራ እንደሚያስገባ አስታውቋል።

የቢሮው ኃላፊ አዋሌ መሀመድ ለኢዜአ እንዳሉት በስማርት ሲቲ ትግበራ አዲስ አበባን ለነዋሪዎቿ ምቹና ዘመናዊ ለማድረግ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ።

በስማርት ሲቲ ትግበራ አገልግሎት አሰጣጡን በቴክኖሎጂ ማስደገፍ መቻሉ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ብለዋል።

በሲቲ ኔት የዲጂታል መሰረተ ልማት ፕሮጀክት 58 ተቋማት፣ 11ዱ ክፍለ ከተሞችና ሁሉም ወረዳዎች እንዲተሳሰሩ መደረጉንም ተናግረዋል።

በከተማዋ 582 አገልግሎቶችን በበይነ መረብ ለመስጠት መለየቱን ተናግረው ከእነዚህ መካከል 278 አገልግሎቶች በበይነ መረብ እንዲሰጡ ማድረግ መቻሉንም ገልፀዋል።

ህብረተሰቡ ጥያቄ የሚያነሳባቸውን አገልግሎቶች በመለየትና ቅድሚያ ትኩረት በመስጠት በበይነ መረብ እንዲተገበሩ መደረጋቸውን አንስተዋል።

ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎትን ለህብረተሰቡ ተደራሽ ማድረግ የሚያስችሉ የስማርት አገልግሎቶችን የማስፋት ስራ ተጠናክሮ እንደቀጠለም አስረድተዋል።

በአዲስ አበባ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ እና ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን የስማርት ኦፊስ ስራ በማከናወን አገልግሎት አሰጣጡን የማዘመን ስራ መከናወኑንና ሰኔ 1 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚመረቅ ገልፀዋል።

የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቶማስ ደበሌ ሁለቱ ተቋማት የሚሰጡትን አገልግሎት ለማዘመን የሪፎርም ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

ስማርት ኦፊስ ለመገንባት የተለያዩ ስራዎች መከናወናቸውን ጠቁመው ከጨረታ ጀምሮ እስከ ቤት ማስተላለፍ ያለውን ሂደት የማዘመን ስራ መሰራቱን ጠቁመዋል።

በተቋማቱ ከፍተኛ አቅም ያለው የዳታ ማዕከል፣ የሶፍትዌር ልማት፣ ዘመናዊ የጂም ግንባታና ሌሎች አገልግሎቶችን የማዘመን ስራ መሰራቱን ጠቅሰዋል።

በተዘረጉት አዳዲስ መሰረተ ልማቶችና በለሙ ሶፍትዌሮች ላይ ሙከራ መደረጉንና ከደህንነት ጋር የተያያዘ ፍተሻ በማከናወን አስተማማኝነታቸውን ማረጋገጥ መቻሉን አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም