የኮሪደር ልማት ስራው የቡታጅራ ከተማን ለስራና ለመዝናኛ ምቹ አድርጓታል - ኢዜአ አማርኛ
የኮሪደር ልማት ስራው የቡታጅራ ከተማን ለስራና ለመዝናኛ ምቹ አድርጓታል

ቡታጅራ፣ ግንቦት 27/2017 (ኢዜአ) ፡-በቡታጅራ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ለስራና ለመዝናኛ ምቹ እንዳደረጋት የከተማዋ ነዋሪዎች ተናገሩ።
በቡታጅራ ከተማ 25 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የኮሪደር ልማት ስራ በህዝቡና በአስተዳደሩ የጋራ ትብብር እየተከናወነ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል።
አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የቡታጅራ ከተማ ነዋሪዎች እንዳሉት እየተሰራ ያለው የኮሪደር ልማት ስራ ከተማዋን ለኑሮ ምቹና ሳቢ እያደረጋት ነው።
ከከተማው ነዋሪዎች መካከል አቶ ሽመልስ ለማ እንዳሉት ነዋሪው ለልማትና ለሰላም የማይደራደርና ከመንግስት ጋር ተባብሮ በመስራት የሚታወቅ ነው።
ለዚህም ህዝቡ የሚጠበቅበትን ግዴታ እየተወጣ ነው ያሉት ነዋሪው የኮሪደር ልማቱ ምቹ የመዝናኛ ስፍራ እንድናገኝ አድርጎናል ብለዋል።
ሌላው አስተያየት ሰጪ አቶ ይሳቅ ፈሪድ በበኩላቸው በአሁኑ ወቅት በከተማው እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት የብስክሌት፣ የተሽከርካሪና የእግረኛ መንገድ በተለያየ ሁኔታ የያዘ በመሆኑ ለእግረኛና ለተሽከርካሪ ምቹ ሁኔታን የፈጠረ ነው ብለዋል።
ከተማዋ ከፍተኛ የንግድ እንቅስቃሴ የሚካሄድባት በመሆኑ ለንግድ ልውውጥ የሚመጡ እንግዶችም ከንግድ ስራቸው ባለፈ በከተማዋ ተጨማሪ ጊዜን እንዲያሳልፉ የኮሪደር ልማቱ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳበረከተም አመልክተዋል።
በኮሪደር ልማቱ የስራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ነዋሪዎች መካከል ወጣት ግዛቸው አብረሃም በግንበኝነት ሙያ በተፈጠረለት የስራ ዕድል ገቢ እያገኘ መሆኑን ተናግሯል፡፡
በኮሪደር ልማቱ ላይ አሻራውን በማሳረፍ የመኖሪያ ከተማው ውብና ሳቢ ተደርጎ እየተገነባ በመሆኑደስተኛ እንዳደረገውም ጠቁሟል።
የቡታጀራ ከተማ ከንቲባ አቶ አብዶ አህመድ በከተማው 25 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የኮሪደር ልማት ሥራ ህብረተሰቡን በማሳተፍ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው በእስካሁኑ ሂደት 8 ነጥብ 3 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነው የስራው ክፍል መጠናቀቁን ተናግረዋል።
በህዝቡና በከተማ አስተዳደሩ ትብብር እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት ሥራ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት እንደተመደበ ጠቁመዋል።
የኮሪደር ልማት ሥራው በሚከናወንባቸው አካባቢዎች ህዝቡ ደስተኛ ሆኖ ንብረቱን በማንሳት የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን ገልጸው ልማቱ በቡታጀራ ከተማ የሚካሄደውን ከፍተኛ የንግድ እንቅስቃሴና የቱሪስት ፍሰት እንዲጨምር ማድረጉን ገልፀዋል።
ስራውም የአረንጓዴ ልማት፣ የመዝናኛ ስፍራዎች፣ የእግረኛ መንገዶች፣ የብስክሌት መንገድና መናፈሻዎችን ባካተተ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ከንቲባው ጠቁመዋል።
በእነዚህ ስራዎች ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ጠቅሰው፣ የመጀመሪያው ዙር የኮሪደር ልማት ሰኔ 30 ተጠናቆ ለምረቃ ይበቃል ብለዋል።