ለውጪ ገበያ ለሚቀርቡ የግብርና ምርቶች መልከዓ ምድራዊ አመላካች ጥበቃ ማድረግ የሚያስችል ዝግጅት እየተከናወነ ነው - የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 26/2017(ኢዜአ)፦ ለውጪ ገበያ ለሚቀርቡ የግብርና ምርቶች መልከዓ ምድራዊ አመላካች ጥበቃ ማድረግ የሚያስችል ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን አስታወቀ።

የመልክዓ ምድራዊ አመላካች የግብርና እና ዕደ-ጥበብ ምርቶች ጥበቃ ላይ ያተኮረ ዓለም አቀፍ ጉባዔ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል።


 

የምርቶች መልከዓ ምድራዊ አመላካች ጥበቃ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለምትታወቅባቸው የግብርና ምርቶች ጣዕምና ልዩ ባህሪ ዕውቅና በመስጠት የተሻለ ዋጋ እንዲያገኙ ያስችላል ተብሏል።

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር) በጉባዔው መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ ለአዳዲስ ፈጠራዎችና ቴክኖሎጂዎች የተለየ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች ነው።

በዚህም ለአምራቾች የተለየ የምርት ዕውቅና መስጠት ፈጠራን ማበረታታት እንደሆነም አንስተዋል።

የአለም አእምሯዊ ንብረት ድርጅት(WIPO) ዳይሬክተር ጀነራል ዳረን ታንግ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በርካታ የግብርና ምርቶችን ለዓለም ገበያ በማቅረብ ብትታወቅም የምርቶቹን መገኛ ቦታና ልዩ ባህሪ የሚያመላክት መልከዓ ምድራዊ ጥበቃ ላይ የህግ ማዕቀፍ ሳታዘጋጅ መቆየቷን ተናግረዋል።

በዚህም የኢትዮጵያ የግብርና ምርቶች ልዩ ጣዕምና ባህሪ በትክክል እንዳይታወቅና አምራቾቹም ተገቢውን የኢኮኖሚ ጥቅም እንዳያገኙ ማድረጉን አመልክተዋል።

እንደ ሀገር ለግብርና ምርቶች መልከዓ ምድራዊ ጥበቃ ማድረግ የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ ማዘጋጀት መጀመሩ ወሳኝና ትክክለኛ እርምጃ መሆኑን ነው ያነሱት።


 

የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ወልዱ ይመስል በበኩላቸው በመገኛ ምንጫቸው ተለይተው የሚታወቁ የግብርና ምርቶች ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ በመሆን የተሻለ ዋጋ ያወጣሉ ብለዋል።

አሁን ላይ በግብርና ምርቶች መገኛና ልዩ ባህሪ ላይ የዳሰሳ ጥናት በማድረግ ዕውቅና የሚያገኙበትን ሥርዓት መዘርጋት የሚያስችል ረቂቅ የህግ ማዕቀፍ ተዘጋጅቷል ብለዋል።

ረቂቅ የህግ ማዕቀፉ የተለያዩ ሀገራት የተሻለ ተሞክሮ ተቀምሮበት ለሚመለከታቸው አካላት እንደሚቀርብ ጠቁመው፤ ከአንድ ዓመት በኋላ ወደ ስራ ይገባል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል።

እንደ ዋና ዳይሬክተሩ ገለጻ፣ ቡናን ጨምሮ ወደ ውጪ የሚላኩ የግብርና ምርቶች ከምንጫቸው በአግባቡ ተለይተውና ዕውቅና ተሰጥቷቸው ወደ ገበያ ባለመቅረባቸው አምራቹ ተገቢውን ጥቅም እንዳያገኝ አድርጓል።

የህግ ማዕቀፉ ተግባራዊ ሲሆን፤ የእያንዳንዱ ምርትን ልዩ ባህሪ የያዘ መጽሃፍ እንዲታተም በማድረግ ገዥው ስለምርቱ በቂ ግንዛቤ ይዞ እንዲገዛና ተመሳስሎና ከሌላ ምርት ጋር ተደባልቆ ከሚመረት ተመሳሳይ ምርት እንዲለይ ያደርጋል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም