የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ምሁራን አምራች ዜጋ በማፍራት በኢኮኖሚያዊ ዕድገት ላይ ጉልህ ሚና እየተጫወቱ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ምሁራን አምራች ዜጋ በማፍራት በኢኮኖሚያዊ ዕድገት ላይ ጉልህ ሚና እየተጫወቱ ነው

አዲስ አበባ፤ግንቦት 26/2017(ኢዜአ)፦የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ምሁራን ክህሎት ያለው አምራች ዜጋ በማፍራት በኢኮኖሚ ልማት ላይ ጉልህ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኙ የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ ገለጹ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስዳደር ’’የበቃ አሰልጣኝ፤ ክህሎት የጨበጠ ወጣት፤ ለበለጸገ ሀገር’’ በሚል መሪ ሃሳብ ከቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ዲኖችና አሰልጣኝ መምህራን ጋር የምክክር መድረክ አካሂዷል።
የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጃንጥራር ዓባይ በመድረኩ ላይ ባለፉት ሁለት ሳምንታት የተለያዩ የሙያ ዘርፎችን ከወከሉ አካላት ጋር ገንቢ ምክክር መደረጉን አስታውሰዋል።
ከቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ምሁራን ጋር የተደረገው መድረክም የመዲናዋን ኢኮኖሚያዊ፣ማህበራዊና ፖለቲካዊ ስኬቶች ማስቀጠል በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ለመምከር ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ የዕድገት ታሪክ የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ምሁራን ለመካከለኛው ኢንዱስትሪ ክህሎት ያላቸው ሙያተኞችን በማፍራት በኢኮኖሚ ልማት ላይ ጉልህ ሚና እየተጫወቱ መሆኑን አስታውቀዋል።
በቀጣይም የኢትዮጵያን የዕድገት ፍላጎትን ታሳቢ በማድረግ ብቃትና ክህሎት ያላቸው ዜጎችን በማፍራት የመዲናዋን ሁለንተናዊ ስኬት ማስቀጠል እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል።
ከቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ዲኖችና አሰልጣኝ መምህራን የሚነሱ ሃሳቦች ለመዲናዋ ዘላቂ ዕድገት አዎንታዊ ሚናን በመወጣት ለፖሊሲ ግብዓትነት ጭምር እንደሚውሉ አስረድተዋል።
የውይይቱ ተሳታፊ የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና አሰልጣኝ መምህራን በመዲናዋ በአጭር ጊዜ በጥራት የተገነቡ ግዙፍና ሰው ተኮር የልማት ስራዎች የሚደነቁ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ያፈሯቸው ክህሎት ያላቸው ሙያተኞችም በኮሪደርና በኢንተርፕራዝ ልማት ላይ አዎንታዊ ሚና እየተጫቱ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
የተቋማቱ መምህራን የሚያነሷቸው የመኖሪያ ቤት፣ የትራንስፖርት፣ የገበያና የተቋማዊ የአሰራር ማሻሻያዎችም ምላሽ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።
ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ በምላሻቸው÷ በመዲናዋ የነዋሪዎችን ጫና የሚያቃልሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችና ሰው ተኮር የልማት ስራዎች መሰራታቸውን አንስተዋል።
በመኖሪያ ቤት ልማት ዘርፍም በተለያዩ አመራጮች ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን ገልጸዋል።
በየትኛውም ኢንቨስትመንትና ኢንተርፕራይዝ ልማት የቴክኒክና ሙያ አሰልጣኞች ክህሎትና ብቃት ያላቸው አምራች ሙያተኞችን ማፍራት እንደሚኖርባቸው አስገንዝበዋል።
በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ጥራቱ በየነ÷ ኢትዮጵያ ፀጋዋን በመጠቀም በሁሉም መስክ ብልጽግናን እንደምታረጋግጥ ጠቅሰው፤ በአጭር ጊዜ የተመዘገቡ የልማት ስኬቶችም ማሳያ ናቸው ብለዋል።
የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ክህሎት የተላበሰ አምራች ዜጋ ማፍራት አለባቸው ብለዋል።