በእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ላይ የሚስተዋሉ ማነቆዎችን በመፍታት የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብርን ውጤታማነት ለማስቀጠል ትኩረት ተሰጥቷል - ኢዜአ አማርኛ
በእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ላይ የሚስተዋሉ ማነቆዎችን በመፍታት የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብርን ውጤታማነት ለማስቀጠል ትኩረት ተሰጥቷል

ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 26/2017(ኢዜአ)፦ በእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ላይ የሚስተዋሉ ማነቆዎችን በመፍታት የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብርን ውጤታማነት ለማስቀጠል እየተሰራ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ።
በሚኒስቴሩ የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አስራት ጤራ(ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በእንስሳት ዝርያ በተለይ የዳልጋ ከብቶችን ዝርያ በማሻሻል የወተት ምርታማነትን ለማሳደግ ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሶዶ ዳልጋ ከብቶች ዝርያ ማሻሻያ ማዕከል የተገነባው የፈሳሽ ናይትሮጂን ማምረቻም ከኮርማ የሚገኘውን ዘር ሳይበላሽ በህይወት ለማቆየትና ከአንዱ ኮርማ የተገኘውን የዘር ፍሬ ለበርካታ ላሞች ለማዳቀል እንደሚያስችል ጠቁመዋል።
ይህም አርሶ አደሩና በእንስሳት ልማት ላይ የተሰማሩ ከሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር የተሻለ ተጠቃሚ እንዲሆኑና የምግብ ዋስትናቸውን እንዲያረጋግጡ ያግዛል ብለዋል።
ቀደም ሲል የእንስሳት ዝርያን በማሻሻል የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት የፈሳሽ ናይትሮጂን እጥረት ከፍተኛ ችግር እንደነበር ያስታወሱት ደግሞ የሶዶ ዳልጋ ከብቶች ዝርያ ማሻሻያ ማዕከል ኃላፊ ምህረቱ ማርቆስ ናቸው።
በአሁኑ ወቅት ማዕከሉ ተገንብቶ ሥራ መጀመሩ የፈሳሽ ናይትሮጂን ምርትን በማሳደግ ችግሩን ሙሉ በሙሉ መፈታቱን ገልጸዋል።
የፈሳሽ ናይትሮጂን ማምረቻው የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ሥራውን በማቀላጠፍ የወተት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ አበርክቶው የጎላ ነውም ብለዋል።
በወላይታ ሶዶ ከተማ በእንስሳት እርባታ ሥራ የተሰማሩት የኤግዞደስ ፋርም ሥራ አስኪያጅ ተሻለ አላጋው(ዶ/ር) ከዚህ ቀደም የፈሳሽ ናይትሮጂን እጥረት በስራቸው ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ሲያሳድር መቆየቱን አስታውሰዋል።
የኮርማውን ዘር ከሩቅ አካባቢዎች ገዝተው በማምጣት ለከፍተኛ ወጪ ሲዳረጉ እንደነበርም ተናግረዋል።
የተገዛው ዘርም በፈሳሽ ናይትሮጂን እጥረት ምክንያት በከንቱ ይባክን እንደነበር ጠቅሰው በከተማው ፈሳሽ ናይትሮጂን መመረቱ በአካባቢው በዘርፉ ለተሰማሩ እፎይታ መስጠቱንና ውጤታማ እንደሚያደርግም ገልጸዋል።
መንግስት የግብዓት እጥረቶችን በመፍታት የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብርን ለማጠናከር እያሳየ ያለው ቁርጠኝነት መጠናከር ለምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ ያበረክታል ነው ያሉት።
በወላይታ ሶዶ ከተማ ከ63 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባው የፈሳሽ ናይትሮጂን ማምረቻ፣ ማቀነባበሪያና ማሰራጫ ማዕከል የፌደራልና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች በተገኙበት በቅርቡ ተመርቆ ሥራ መጀመሩ የሚታወስ ነው።