ከቁንዶ በርበሬ ቅመም ምርት ሽያጭ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችን እያደገ ነው

ሚዛን አማን፤ግንቦት 21/2017 (ኢዜአ)፦የቁንዶ በርበሬ ቅመምን በማምረት ከምርት ሽያጩ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መሆኑን በሸካ ዞን የየኪ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ።

የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል መነሻ ዘር ከውጭ በማምጣት ያላመደው የቁንዶ በርበሬ ቅመም ምርታማና ለአካባቢው አየር ጸባይ ተስማሚ መሆኑንም አርሶ አደሮቹ ገልጸዋል።

አስተያየታቸውን ከሰጡ አርሶ አደሮች መካከል በየኪ ወረዳ የፊዴ ቀበሌ ነዋሪ ዓይናቸው ካሳሁን፥ በ2 ነጥብ 5 ሄክታር ማሳ ላይ የሚያመርተውን ቁንዶ በርበሬ ለገበያ በማቅረብ ገቢውን እያሳደገ መሆኑን ለኢዜአ ተናግሯል።

ከቁንዶ በርበሬ ማሳው በዓመት እስከ 20 ኩንታል ምርት እንደሚያገኝ ገልጾ፥ዘንድሮ ካለው ምቹ የአየር ሁኔታ በመነሳት የተሻለ ምርት እንደሚጠብቅ አመልክቷል።

በቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል ድጋፍና ክትትል ለተሻለ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት መድረሱን የገለጸው ወጣቱ አርሶ አደር በቀጣይም ልማቱን ለማስፋፋት ግማሽ ሄክታር ማሳ ማዘጋጀቱን ጠቁሟል።

ሌላው የአሮጌ ብርሃን ቀበሌ ነዋሪ አየነው አለልኝ፥ የቁንዶ በርበሬ ልማት ሥራ ባከናወነባቸው ሦስት ዓመታት ውስጥ ከልማቱ በተጨማሪ ችግኝ በማዘጋጀት ለሌሎች አርሶ አደሮች በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን እያሳደገ መሆኑን ተናግሯል።

ካለው አንድ ሄክታር የቁንዶ በርበሬ ማሳ እስከ 10 ኩንታል ምርት እንደሚጠብቅም ገልጿል።

የቁንዶ በርበሬ ዋጋ ከሁለት ዓመታት በፊት ከነበረው በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ በመምጣቱ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግሯል።

በቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል መነሻ ቴክኖሎጂ ብዜትና ዘር ምርምር የሥራ ሂደት አስተባባሪ አቶ በኃይሉ መኮንን፥ ማዕከሉ የግብርና ቴክኖሎጂ ውጤቶችን ለአርሶ አደሮች እያቀረበ መሆኑን ተናግረዋል።

ከዚህ በተጨማሪ አዳዲስ የቅመማ ቅመም ዘር ከማዕከሉ የሚወስዱ አርሶ አደሮችን የሥራ እንቅስቃሴ በቅርበት በመከታተልና በመደገፍ ለውጤት ለማብቃት እንደሚሰራ ገልጸዋል።

በዚህም የተሻለ የቅመማ ቅመም ማሳ በአርሶ አደሮች ጓሮ እየታየ መሆኑን ጠቅሰው፥ማዕከሉ መሰል ተግባሩን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

የቴፒ ብሔራዊ የቅመማ ቅመም አስተባባሪና ተመራማሪ አቡኪያ ጌቱ፥ የቁንዶ በርበሬ ምርት በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ እና በጋምቤላ ክልሎች በሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች እየተስፋፋ መሆኑን አመልክተዋል።

የቁንዶ በርበሬ ልማት ከዛፎች ጋር ትስስር ስላለው ተፈጥሮን የመጠበቅ ጠባይ አለው ያሉት ተመራማሪው፥ከአንድ ሄክታር የቁንዶ በርበሬ ማሳ ከሚሰበሰብ ምርት ከ2 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

በመሆኑም አርሶ አደሩን ከልማቱ ይበልጥ ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም