ህብረተሰቡ ትውልድ ተሻጋሪ የመሰረተ ልማት ስራዎችን መጠበቅና መንከባከብ አለበት- የምክር ቤት አባላት - ኢዜአ አማርኛ
ህብረተሰቡ ትውልድ ተሻጋሪ የመሰረተ ልማት ስራዎችን መጠበቅና መንከባከብ አለበት- የምክር ቤት አባላት

ባህር ዳር፤ግንቦት 10/2017 (ኢዜአ)፦በባህር ዳር ከተማ እየተገነቡ የሚገኙ ትውልድ ተሻጋሪ የመሰረተ ልማት ስራዎችን ህብረተሰቡ ሊጠብቃቸውና ሊንከባከባቸው ይገባል ሲሉ የከተማዋ አስተዳደር ምክር ቤት አባላት አሳሰቡ።
የምክር ቤት አባላቱ በከተማዋ የሚካሄደውን የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በከተማዋ እየተገነቡ የሚገኙ የልማት ስራዎችን ተዘዋውረው ጐብኝተዋል።
የምክር ቤቱ አባል የሆኑት ሲስተር አዲስ ዓለም ካሴ በወቅቱ እንዳሉት፥ በከተማዋ እየተገነቡ ያሉ የልማት ስራዎች ትውልድ ተሻጋሪና የአመራር ቁርጠኝነትን በግልጽ የሚያንጸባርቁ ናቸው።
የከተማዋ አመራር የልማት ስራዎችን በጥራትና በስፋት ማከናወኑ ኃላፊነትን በአግባቡ ከተጠቀሙበት ህዝብን ለማገልገል ያለውን ዋጋ የሚያሳይ ነው ብለዋል።
ለዚህም በከተማዋ እየተገነቡ ያሉ የአረንጓዴ ልማት ስፍራዎች፣ የኮሪደር ልማት፣ የአስፋልት መንገዶችና ሌሎች የልማት ስራዎች ትልቅ ማሳያ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ግንባታዎቹ የባህር ዳር ከተማን ለቱሪስትና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ ለማድረግ የሚያስችሉ በመሆናቸው ነዋሪዎች የመንከባከብና የመጠበቅ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡም ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል።
ሌላው የምክር ቤት አባል አቶ ዘላለም ጌታሁን በበኩላቸው፥ በከተማዋ እየተገነቡ ያሉ የአስፋልት መንገዶች የከተማዋን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የሚያፋጥኑ ናቸው ብለዋል።
ምክር ቤቱ በከተማዋ የሚከናወኑ የልማት ስራዎችን ክትትል እንደሚያደርግ ጠቁመው፥ ህብረተሰቡ የልማት ስራዎቹ ለረጅም ጊዜ አገልግሎት እንዲሰጡ መጠበቅና መንከባከብ ይጠበቅበታል ብለዋል።
የከተማዋ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው እንደገለጹት፥ የባህር ዳር ከተማን የኢኮኖሚና ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የሚያስችሉ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ ነው።
ሰላምን ማጽናትና ዘላቂ ከማድረግ ጎን ለጎን የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመው፥ የልማት ስራዎቹ ተፈጥሮ የቸራትን የባህር ዳር ከተማ የበለጠ ውብ ለማድረግ የሚያስችሉ መሆናቸውንም ተናግረዋል።
ትናንት የተጀመረው የከተማ አስተዳደሩ ምክር ቤት 29 መደበኛ ጉባኤም ዛሬ እንደሚጠናቀቅ ታውቋል።