በመስኖ ታግዘን ከምናከናውነው የግብርና ሥራ ውጤታማ ለመሆን ጠንክረን እየሰራን ነው-አርሶ አደሮች - ኢዜአ አማርኛ
በመስኖ ታግዘን ከምናከናውነው የግብርና ሥራ ውጤታማ ለመሆን ጠንክረን እየሰራን ነው-አርሶ አደሮች

ወልቂጤ፤ግንቦት 8/2017 (ኢዜአ)፦በአካባቢያቸው በተገነቡ የመስኖ ፕሮጀክቶች ታግዘው ከሚያከናውኑ የግብርና ሥራ ውጤታማ ለመሆን ተግተው እየሰሩ መሆኑን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የጉራጌ እና የየም ዞኖች አርሶ አደሮች ገለጹ።
አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ አርሶ አደሮች መካከል በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ጌታቸው ፈቀደ በአካባቢው በመንግስት ድጋፍ የተገነባው የመስኖ ፕሮጀክት የግብርና ምርታማነታቸውን በማሳደግ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ዕድል ፈጥሯል።
ቀደም ሲል ከወንዝ ውሃ በጄኔሬተር ስበው ሲያለሙ ለብዙ ወጪና ብክነት ሲዳረጉ እንደነበር አስታውሰዋል።
መንግስት የገነባው የሬቡ መስኖ ፕሮጀክት በአካባቢያቸው አቋርጦ ስለሚያልፍ ውሃውን ጠልፈው የተለያዩ ሰብሎችን በማልማት ምርታማነታቸውን ለማሳደግ ጠንክረው እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።
ለግብርና ስራችን ከመስኖ በተጨማሪ አማራጭ ቴክኖሎጂዎች መንግስት ማመቻቸቱ ልማቱን በተሻለ ለማከናወን አነሳስቶናል" ያሉት ደግሞ ሌላኛው የወረዳው አርሶ አደር ኑርአዲስ ሁሴን ናቸው።
ለመስኖ ግንባታ የሚሆን የወንዝ አማራጭ በሌለባቸው አካባቢዎች መንግስት በፀሐይ ሀይል የሚሰራ የውሃ መሳቢያ ሞተር በማምቻቸቱ የግብርና ሥራቸውን አስፋፍተው ለማከናወነ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።
በየም ዞን ደሪ ሳጃ ዙርያ ወረዳ የኮሻ መስኖን በመጠቀም በዓመት ሦስት ጊዜ እና ከዚያ በላይ ማምረት መጀመራቸውን የተናገሩት ደግሞ አርሶ አደር አጥናፉ ወልደኢየሱስ ናቸው።
ከዚህ ቀደም ሥራ በማጣት ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ሲዳረጉ እንደነበር አስታውሰው በአሁኑ ወቅት መስኖ በመጠቀም ማሽላ፣ በቆሎ፣ አትክልት እና ፍራፍሬ እያለሙ መሆናቸውንና የተሻለ ገቢ ለማግኘት ጠንክረው እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።
ሌላኛው አርሶ አደር ዘሪሁን ጋሼ መስኖን ጨምሮ በዓመት ከሦስት ጊዜ በላይ አትክልትና ፍራፍሬ በማምረትና ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግረዋል።
ከዚህ በተጨማሪ በአጠገባቸው የሚያልፈውን የመስኖ ውሃ ተጠቅመው በሚያዘጋጁት ኩሬ ዓሣ ለማምረት ቅድመ ዝግጅት እያደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመስኖ ተቋማት ልማትና አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ካሳዬ ተክሌ እንዳሉት ፣ በክልሉ በበጀት ዓመቱ ከ393 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ 16 አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተካሄደ መሆኑን ተናግረዋል።
እስካሁንም 10 የመስኖ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ሙሉ በሙሉ ለአገልግሎት መብቃታቸውን ጠቅሰው፣ ከወንዝ መጥለፍ ለማይችሉ አካባቢዎች በጸሐይ ሀይል የሚሰሩ 70 የውሃ መሳቢያ ሞተሮች መቅረባቸውን ጠቁመዋል።
በክልሉ ያለውን የውሃና የመሬት ሀብት በአግባቡ በመጠቀም የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን ጠቅሰው፣ በዚህም አርሶ አደሩ ከመነቃቃት ባለፈ ውጤት እያስመዘገበ ይገኛል ብለዋል።
የመስኖ ተቋማት በዘላቂነት አገልግሎት እንዲሰጡ ለማስቻልም ከማህበረሰቡ ጋር በመወያየት የአጠቃቀም መመሪያ ተዘጋጅቶ ወደስራ መገባቱን አስረድተዋል።