መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ ሽግግር ትልቅ እርምጃ ነው -ሚኒስትሮች - ኢዜአ አማርኛ
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ ሽግግር ትልቅ እርምጃ ነው -ሚኒስትሮች

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 24/2017(ኢዜአ)፦መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ ሽግግር ትልቅ እርምጃ መሆኑን ሚኒስትሮች ተናገሩ፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ጨምሮ ሚኒስትሮችና የፌዴራል ተቋማት አመራር አባላት መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ጎብኝተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት(ኢዜአ) በዚሁ ወቅት ያነጋገራቸው ሚኒስትሮች ማዕከሉ የመንግስት አገልግሎትን በከፍተኛ ሁኔታ የሚያቀላጥፍ መሆኑን አንስተዋል፡፡
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን የተቀናጀ አገልግሎት ለተገልጋዩ መስጠት የሚያስችል ትልቅ ውጤታማ ስራ መሆኑንም ገልጸዋል።
የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በማደራጀት ወደ ስራ መገባቱ በአገሪቱ የታለመውን ለውጥ ለማምጣት ወሳኝ ነው፡፡
ማዕከሉ ቅሬታ ይቀርብባቸው የነበሩ አገልግሎቶችን ወደ ዲጂታል በማስገባት የተቀላጠፈ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ትልቅ እርምጃ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ ሽግግር ትልቅ እርምጃ መሆኑን ሚኒስትሩ አስገንዝበዋል፡፡
የፍትህ ሚኒስትር ሀና አርዓያሥላሴ በበኩላቸው፥ መሶብ ለብዙ ግዜ በመንግስት ተቋማት የነበሩ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን የሚፈታ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዘመኑን የዋጀ ቴክኖሎጂን አቀናጅቶ የያዘ ትልቅ ተቋም መሆኑን ገልጸው፥ ስራዎች በአግባቡ ከተመሩ ትልቅ ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል ያስመሰከረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የሰላም ሚኒስትር መሀመድ እድሪስ፤ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መንግስት ለሰው ተኮር አገልግሎት የሰጠው ትኩረት የተግባር ማረጋገጫ ነው ብለዋል።
ህብረተሰቡ ባልተንዛዛ ቢሮክራሲ እንዲሁም በተቀላጠፈ መንገድ አገልግሎት እንዲያገኝ የሚያደርግ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
በአጠቃላይ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በአገሪቱ የአገልግሎት አሰጣጥ እንደ ታሪክ እጥፋት የሚቆጠር ትልቅ ስራ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ በበኩላቸው፥ መሶብ አገልግሎትን ከማዘመን ባለፈ ተጠያቂነትን ለማስፈን የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ስራዎችን በፍጥነት በመጨረስ መተግበር እንደሚቻል ያሳየ መሆኑን አንስተው፥ ለጤናው ዘርፉ አገልግሎት አሰጣጥም ተሞክሮ የሚወሰድበት ነው ብለዋል።