በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ልማት ሽግግርን የሚያሳልጥ ምቹ የአሰራር ምህዳር ተፈጥሯል -የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር - ኢዜአ አማርኛ
በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ልማት ሽግግርን የሚያሳልጥ ምቹ የአሰራር ምህዳር ተፈጥሯል -የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ልማት ሽግግርን የሚያሳልጥ ምቹ የአሰራር ሥርዓተ ምህዳር መፈጠሩን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ (ዶ/ር) ገለጹ።
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በኢትዮጵያ ቁልፍ የልማት ዘርፎች ላይ የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግርን የማሳለጥ ዓላማን ያነገበ የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ በአዲስ አበባ አካሂዷል።
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ (ዶ/ር) በመድረኩ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር እንደገለጹት፤ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ልማትን ለማሳለጥ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል።
የዲጂታል ቴክኖሎጂ ልማትን ለማስፋትም ከተቋማት ጋር በመተባበር በመንግስትና የግል አጋርነት ጭምር ቀጣይነት ያላቸው ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አስረድተዋል።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)፥ የዜጎችን የቴክኖሎጂ ዕውቀትና ክህሎት ለማበልጸግ ተግባራዊ እየተደረገ የሚገኘው የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠናም ወሳኝ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝም ተናግረዋል።
ዜጎችም በአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠና ላይ በንቃት በመሳተፍ የቴክኖሎጂ ዕውቀትና ክህሎታቸውን ማበልጸግ የሚችሉበትን ዕድል መጠቀም እንዳለባቸው መልዕክት አስተላልፈዋል።
የቴክኖሎጂ አቅም የመምራት፣የማቀናጀትና የመገንባት መሪነት ሚና በመወጣት ስኬታማ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ልማትና ሽግግር ሥነ-ምኅዳር መፍጠር እንደተቻለም ተናግረዋል።
በዚህም በስታርት አፕ፣በሰው ሃብት ልማት፣ በፖሊሲ የሕግ ማዕቀፍ ዝግጅትና አሰራር የመሰረተ ልማት ዝርጋታ ምቹ የቴክኖሎጂ ሽግግር ልማት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።
ባለፉት ሰባት ዓመታትም በቴክኖሎጂ ልማት ሽግግር የተከናወነው ተግባራት ከሀገር በቀል እስከ ዓለም አቀፍ ድረስ ዕውቅና የተቸራቸው ስራዎች መከናወናቸውን አስረድተዋል።
በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ክፍል መሪ ስራ አስፈፃሚ ተክለማርያም ተሠማ(ዶ/ር) በበኩላቸው፥ በኢትዮጵያ የ10 ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ በሁሉም መስክ ሀገር በቀል የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ትኩረት ተሰጥቶታል።
በዚህም ሀገር በቀል የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግርን ማሳለጥ የሚያስችል ፖሊሲን በመተግበር ምርታማነትን ማሻሻል የሚያስችሉ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል።
በቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር የተከናወነው ተግባርም በግብርና፣በጤና፣ በትምህርትና ሌሎች መስኮች የምርታማነትና የአገልግሎት መሻሻል እየተመዘገበ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
በባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዮት የቴክኖሎጂ ኢንኩቤሽንና ኮመርሻላይዜሽን መሪ ሥራ አስፈፃሚ ዑስማን ኡመር፤ የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግርን ለማሳለጥ ከግሉ ዘርፍ፣ ከከፍተኛ ትምህርትና የምርምር ተቋማት ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በዚህም በግብርና፣በኢንዱስትሪ፣ ጤናን ጨምሮ በርካታ የቁስና ተፈጥሮ ሳይንሱን በማሰናሰል በባዮ ቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ላይ ቀጣይነት ያለው ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል።