የክህሎት ውድድሩ ዘርፉን መምራት የሚችል የሰው ሃይል ለማፍራት ያግዛል

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦በተማሪዎች መካከል የሚካሔደው የክህሎት ውድድር  ዘርፉን መምራት የሚችል ብቃት ያለው የሰው ሃይል ለማፍራት እንደሚያግዝ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ገለፁ።

አራተኛው ሀገር አቀፍ የክህሎት ውድድር እና 12 ኛው የቱሪዝምና እንግዳ ተቀባይነት ሳምንት ማስጀመርያ መርኃ ግብር እየተከናወነ ይገኛል።

በመርኃ ግብሩ ላይ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ፣ የቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ነጋሽ እንዲሁም የቱሪዝም ሚኒስቴር ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።

የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በየጊዜው የሚካሔደው የክህሎት ውድድር በዘርፉ ብቃት ያለው የሰው ሃይል ለማፍራት ትልቅ አቅምን የሚፈጥር ነው።

የክህሎት ውድድሩ የሚሳተፉ ተማሪዎች የተሻለ አቅም ይዘውና ነጥረው እንዲወጡ የሚያግዝ መሆኑንም አንስተዋል።

በተጨማሪም ተማሪዎቹ በሀገር አቀፍ እና በአለም አቀፍ ውድድሮች ላይ የመሳተፍ እድል እንዲኖራቸው ያደርጋል ነው ያሉት።

ተወዳዳሪዎቹ ሀገራቸውን በመወከል በአለም መድረክ እንዲወዳደሩ የሚያስችል እድል እንደሚያስገኝላቸውም  ጠቅሰዋል።

የቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ነጋሽ በበኩላቸው፤ኢንስቲትዩቱ የቱሪዝም ዘርፉ  ክህሎት ባላቸው ዜጎች እንዲመራ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል።

አራተኛው ሀገር አቀፍ የክህሎት ውድድር እና 12ኛው የቱሪዝምና እንግዳ ተቀባይነት ሳምንት "ብሩህ አእምሮዎች በክህሎት የበቁ ዜጎች" በሚል መሪ ሀሳብ ከዛሬ ሚያዝያ 21 እና 22 ቀን 2017 ዓም ይካሄዳል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም