ሀገራችንን የመገንባት የማነጽና የማስዋብ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
ሀገራችንን የመገንባት የማነጽና የማስዋብ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 15/2017(ኢዜአ)፦ ሀገርን የመገንባት የማነጽና የማስዋብ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የካዛንቺስ የኮሪደር ልማት ስራን በትላንትናው እለት መርቀዋል።
ከጥቂት ወራት በፊት ካዛንቺስ የነበረው መልክ ዛሬ ከሚታየው በእጅጉ የተራራቀና ለእይታም ሆነ ለኑሮ በብዙ መልኩ የማይመች እንደነበር አንስተዋል።
የሁለተኛው ዙር የኮሪደር ልማት ካዛንቺስን ያካተተ ሆኖ መጀመሩን ገልጸው፤ በጥቂት ወራት ውስጥም በአካባቢው የተገኘው ውጤት በእጅጉ የሚያኮራ ስራ ነው ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከካዛንቺስ የተነሱ ወገኖች ያሉበትን ሰፈር መመልከታቸውን አስታውሰው፤ ቀደም ሲል ሲኖሩበት የነበረው ከአዲሱ የኑሮ ልምምድና የአኗኗር ዘዬ አኳያ ሲታይ በእጅጉ የተሻለ መሆኑን ገልጸዋል።
ነዋሪዎቹ አሁን ያለው ኑሯቸው የተሻለ መሆኑን ማረጋገጣቸውንም ጠቅሰዋል።
በየትኛውም ሀገር የሚታየው ዘመናዊነት፣ ለውጥና መሻሻል የሚገለጸው በዚህ መንገድ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የዘመኑ የሚባሉ ከተሞች አረንጓዴና ንጹህ የሆኑ ከተሞች መሆናቸውን አብራርተዋል።
የከተማችን ነዋሪዎች መገንዘብ ያለባቸው ከነበርንበት አውድ ሁኔታ ወደ ሚያምረው ሁኔታ ለመውጣት እልህ አስጨራሽ ትጋት ይጠይቃል ሲሉም ገልጸዋል።
ሀገራችንን ለማሳደግና ልጆቻችን ተስፈኞች እንዲሆኑ የበለጸገች ሀገር መስራት እንዲችሉ የተከፈለ ዋጋ መሆኑንም መረዳት እንደሚገባ ተናግረዋል።
ሀገራችንን የመገንባት የማነጽ የማስዋብ ስራው ተስፋችንን፣ ህልማችንንና ንግግራችንን ወደ መሬት አውርዶ የማሳየቱ ጉዳይ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል።
ለዚህም በየደረጃው ያሉ አመራሮች በትጋት በመፍጠርና በመፍጠን መስራት እንደሚገባቸው አሳስበዋል።
በአሁኑ ወቅት ትጋት አስፈላጊ መሆኑን ገልጸው፤ በትጋት አንድ ደረጃ ስንደርስ የሚቀጥለውን ማለም እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል።